በወቅቱ የተጨዋቾች ዝውውር ላይ ዝምታን የመረጡት መቐለ 70 እንደርታዎች የአንተነህ ገብረክርስቶስ፣ሙልጌታ ወልደጊዮርጊስ፣አሸናፊ ሃፍቱ፣ክብሮም አፅብሃ እና ሶፈንያስ ሰይፈ ውል አራዝመዋል።
በ2010 ምዓም አናብስቶቹን የተቀላቀለው አንጋፋው የግራ መስመር ተከላካይ አንተነህ ገብረክርስቶስ ለአራተኛ ተከታታይ ዓመት ከክለቡ ጋር ሚያቆየውን ውል ሊፈርም ችሏል።
ሁለተኛው ተጨዋች ውሉን ያራዘመው ሙሉጌታ ወልደጊዮርጊስ ነው።በ2011 ክለቡን ዳግም ከተቀላቀለ በኃላ የቡድኑ ወሳኝ ተጨዋች መሆን የቻለው ሙሉጌታ በቀጣይ ዓመትም የገብረመድህን ኃይሌ የመሀል ክፍል ሚመራ ይሆናል።
- ማሰታውቂያ -
በኮረና ቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት በተቋረጠው የ2011 የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ላይ ደምቀው ከወጡት ወጣት ተጨዋቾች መሀከል ሚሰለፈው አሸናፊ ሀፍቱ ሌላኛው ውሉን ያራዘመ ተጨዋች ነው።በቀኝ መስመር አማካይ እና ተከላካይ ሆኖ መጫወት ሚችለው አሸናፊ በቀጣይ ዓመታት የቡድኑ ወሳኝ ተጨዋች ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።
መቐለ 70 እንደርታዎች ወደ ፕሪምየር ሊጉ ሲያድጉ የቡድኑ የኃላ ደጀን የነበረው ሶፈንያስ ሰይፈ በክለቡ ለ5ተኛ ዓመት ሚያቆየውን ውል ፈርሟል።ከወሳኝ ግብ ጠባቂያቸው ፊሊፕ ኦቮኖ ጋር የመለያተቸው ነገር እውን የመሰለው መቐለዎች የሶፈንያስ ሰይፈ ውል ማራዘማቸው ለክለቡ ትልቅ እፎይታ ነው።
አምስተኛው ውሉን ያራዘመው ተጨዋች ክብሮም አፅብሃ ነው።ከሰሎዳ ዓድዋ ጋር ባሳለፈው የተሳካ ጊዜ ሚታወሰው ወጣቱ አጥቂ ክብሮም ባሳለፍነው ዓመት መቐለ 70 የተቀላቀለ ሲሆን በሚቀጥለው ዓመትም ከቡድኑ ጋር ሚቀጥል ይሆናል።