በቶታል ካፍ ሻምፒዬንስ ሊግ ጨዋታ ቅዱስጊዬርጊስ በሜዳው ከዩጋንዳው ካፓላ ሲቲ (ኬሲሲኤ) ጋር ያለ ግብ አቻ ተለያይቷል፡፡
ፈረሰኞቹ ለ10ኛ ጊዜ እየተሳተፉበት ባለው የቶታል ካፍ ሻምፒዬንስ ሊግ ቅድመ ማጣሪያ ጨዋታ የደቡብ ሱዳኑን አልሰላም ዋኡን በፎርፌ ሲያሸንፉ፡ የዛሬው ተጋጣሚያቸው ካፓላ ሲቲ የማዳጋስካሩ ስናፕስ ስፓርት ክለብ ላይ ከሜዳቸው ውጭ ባስቆጠሩት ጎል በመርታት ከቅዱስ ጊዬርጊስ ጋር ተገናኝተዋል፡፡
ልክ 10:00 ሲል በጀመረው የቶታል ካፍ ሻምፒዬንስ ሊግ የቅዱስ ጊዬርጊስና የካፓላ ሲቲ ጨዋታ ፡የአዲስ አበባ ስታዲዬም በፈረሰኞቹ ደጋፊዎች ደምቆ አምሽቷል፡፡
ፈረሰኞቹ በኘሪሚዬር ሊጉ በተለመደው የ4-3-3 ፎርሜሺን ወደ ሜዳ ሲገቡ ተጋጣሚያቸው ኬሲሲኤ በ3-4-3 ፎርሜሺን ሲጫዎት፡ባለሜዳዎቹ ፈረሰኞቹ ጨዋታው በሜዳቸው ቢሆንም ለደጋፊዎቻቸው የሚመጥን እንቅስቃሴ አድርገው አምሽተዋል ለማለት አያስደፍርም፡፡
በጨዋታው መጀመሪያ አጋማሽ በቀኝ መስመር አዘንብለው ወደ ተጋጣሚያቸው የግብ ክልል ለመግባት የተጫዎቱት ፈረሰኞቹ ረጃጂም ኳሶችን ለአጥቂ ክፍሉ በማሻገር የግብ ዕድል ለመፍጠር ቢሞክሩም ውጤታማ አልነበሩም፡፡በኳስ ቅብብሎሹም ቢሆን ስኬታማ ሳይሆኑ የዋሉት ባለሜዳዎቹ በ6ኛው ደቂቃ በአቡበከር ሳኒ እና በ10ኛው ደቂቃ በአበባው ቡጣቆ አማካኝነት በተጨማሪም በአማራ ማሌ የግብ ዕድል ቢፈጥሩም ሳይጠቀሙበት ቀርተዋል፡፡
- ማሰታውቂያ -
ፈረሰኞቹ ተጋጣሚያቸውን ኳስ በመንጠቅ በኩል የተሻሉ ቢሆኑም ከመከላከል ወደ ማጥቃት የሚያደርጉት ሽግግር ፍጥነት የሌለውና ደካማ ሁኖ አምሽቷል፡፡የተከላካይ ክፍሉ ከአማካኝ ክፍሉ ቅንጂት አልነበረውም ፡፡ለአጥቂ ክፍሉ የሚላኩት ኳሶች የፊት መስመሩ ያለአግባብ ጉልበት እንዲያባክን የሚዳርጉርጉ ኳሶች ሲሻገሩ አብዱልከሪምና ጋዲሳ ሲባክኑ ተመልክተናል፡፡
ቅዱስ ጊዬርጊስ በሁለተኛው አጋማሽ ጋዲሳን በታደለ፡በጉዳት ከሜዳ ለበርካታ ወራት እርቆ የቆየውን ሳላዲን ሰይድ በአቡበከር በመቀየር ወደ ሜዳ በማስገባት የተጨዋቾ እና የፎርሜሺን ለውጥ በማድረግ ጎል ለማግባት የተጫዎቱ ሲሆን በ60ኛው ደቂቃ አማራ ማሌ ለማግባት የሞከረበት፡ሳላ በ76ኛውና 93ኛው ደቂቃ የተሻለ የግብ ማግባት ሙከራ ቢያደርግም እንዳለመታደል ሆኖ ኳስና መረብን ማገናኘት ሳይችል አምሽቷል፡፡
እንግዳው ቡድን ኬሲሲኤ ኳስን ተቆጣጥረው መጫዎት ላባይችሉም የጨዋታውን ፍጥነት በመጨመርና በማቀዝቀዝ በሚፈልጉት ቴንፖ በማስኬድ አልፎ አልፎ የግብ ዕድሎችን በአማካኙ ኪዛ ሙስጦፋና በአጥቂው ናሲምባቢ ዴሪክ ተደጋጋሚ ሙከራዎችን ሲያደርጉ በሁለተኛው አጋማሽ ተከላካዩ ኪዋኒ ቲሞቲ በ59 ደቂቃ ሞክሮ ኳስን የግቡ ቋሚ የመለሰበት አጋጣሚ የስታዲየሙን ተመልካችም ያስደነገጠ ሙከራ ነበር፡፡
በሜዳውና በደጋፊዎቹ ፊት የተጫዎተው ቅ/ጊዬርጊስ የ1994ቱን ታሪክ መድገም ሳይችል በሜዳው ያለ ግብ አቻ መለያየቱ ፡የቀጣዩ የመልስ ጨዋታ ከሜዳው ውጭ ካፓላ ላይ የሚደረግ መሆኑ የስፖርት ቤተሰቡን ስጋት ውስጥ ከቷል፡፡
የቅዱስ ጊዬርጊስና ካፓላ ሲቲ (ኬሲሲኤ) የመልስ ጨዋታ ከ10 ቀናት በሇላ በዩጋንዳዋ ዋና ከተማ ካምፓላ ስታር ታይምስ ስታዲዬም የሚደረግ ይሆናል፡፡