በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 4ኛ ሳምንት የመጨረሻ 1ጨዋታ ዛሬ የተደረገ ሲሆን በዛሬው ዕለት ኢትዮጵያ ቡና ከ ሀዋሳ ከተማ ጋር የነበረውን ጨዋታ በዚህ ሪፖርት ለእናንተ እንዲስማማ አድርገን አቅርበንላችኋል።
በሊጉ ሁለት በተለያየ አቋም ላይ በሚገኙት ቡድኖች መካከል የተደረገው ይህ ጨዋታ በአዲስ አበባ ስታዲየም ተካሂዶ በኢትዮጵያ ቡና 4-1 በሆነ ሰፊ ውጤት አሸናፊነት ተጠናቋል። ኢትዮጵያ ቡና በሊጉ የመጀመሪያውን ድል ለማስመዝገብ ሀዋሳ ከተማ ደግሞ ከመሪዎቹ ተርታ ላለመራቅ ያደረጉት ጨዋታ በመሆኑ በደጋፊዎቻቸው ዘንድ በጉጉት እንዲጠበቅ አስችሎታል።
- ማሰታውቂያ -
ጨዋታው እንደተጀመረ በተደጋጋሚ ወደ ተቃራኒ የግብ ክልል መድረስ የቻሉት ቡናዎች ተደጋጋሚ ሙከራ ማድረግ ችለው ነበር። 9ኛው ደቂቃ ላይ የኢትዮጵያ ቡናው አቤል ከበደ የሞከረው ኳስ በተከላካዮች ተመልሷል። 11ኛው ደቂቃ ላይ የሀዋሳ ከተማው ብሩክ በየነ ጥሩ ኳስ አግኝቶ ሞክሮት ወደ ውጭ ወጥቶበታል። ከዚህች ሙከራ 4ደቂቃ በኋላ 15ኛው ደቂቃ የኢትዮጵያ ቡናው እንዳለ ደባልቄ ግብ አስቆጥሮ ቡድኑን ቀዳሚ ማድረግ ችሏል። በተደጋጋሚ ጫና መፍጠር የቻሉት ኢትዮጵያ ቡናዎች 31ኛው ደቂቃ ላይ እንዳለ ደባልቄ የሞከረው ኳስ የሀዋሳው ግብ ጠባቂ ቤሌንጋ ኢኖህ አድኖበታል። ከዚህች ሙከራ 4ደቂቃዎች በኋላ 35ኛው ደቂቃ ላይ አቤል ከበደ ግብ አስቆጥሮ የመጀመሪያው አጋማሽ በኢትዮጵያ ቡና 2-0 መሪነት ተጠናቋል።
በሁለተኛው አጋማሽ የተቀዛቀዘ ጨዋታ የተስተዋለ ሲሆን ኢትዮጵያ ቡና ሙሉ የጨዋታ ብልጫ መውሰድ ችሎ ነበር። ይህንንም ተከትሎ የሀዋሳ ከተማን ተከላካይ ሲያስጨንቁ ተስተውለዋል። 65ኛው ደቂቃ ላይ በጨዋታው ጥሩ እንቅስቃሴ ማድረግ የቻለው የኢትዮጵያ ቡናው አቤል ከበደ የሞከረውን ኳስ የሀዋሳው ግብ ጠባቂ በግሩም ሁኔታ አውጥቶበታል። ከዚህች ሙከራ 5ደቂቃዎች በኋላም 70ኛው እንዳለ ደባልቄ ለራሱ 2ኛ ለቡድኑ ደግሞ 3ኛ ግብ አስቆጥሯል።
81ኛው ደቂቃ ላይ የሀዋሳው መስፍን ታፈሰ ጥሩ አጋጣሚ አግኝቶ የግቡ አግዳሚ መልሶበታል። 86ኛው ደቂቃ ላይ የተገኘውን ፍ.ቅ.ም እንዳለ ደባልቄ ወደ ግብነት ቀይሮት የቡናን መሪነት ወደ 4-0 አሳድጓል። ጨዋታው በዚህ ውጤት ተጠናቀቀ ተብሎ ሲጠበቅ 90ኛው ደቂቃ ላይ ብሩክ በየነ ለሀዋሳ ግብ ማስቆጠር ችሎ የነበረ ቢሆንም ከማስተዛዘኛ ያለፈ መሆን አልቻለም። ውጤቱንም ተከትሎ ኢትዮጵያ ቡና በ5ነጥቦች 9ኛ ደረጃ ላይ ሲገኝ ሀዋሳ ከተማ ከኢትዮጵያ ቡና በ2 ነጥቦች ከፍ ብሎ በ7 ነጥቦች 5ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
ሊጉን ወልዋሎ አ.ዩ. በ10 ነጥቦች ሲመራ ፋሲል ከተማ፣ ባህርዳር ከተማ፣ ሀዋሳ ከተማ እና መቐለ 70 እንደርታ በእኩል 7ነጥቦች በግብ ክፍያ ተበላልጠው ከ2ኛ እስከ 5ኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል። የኮከብ ጎል አግቢነቱን ደግሞ የፋሲል ከተማው ሙጂብ ቃሲም እና የኢትዮጵያ ቡናው እንዳለ ደባልቄ በ4 ግቦች ሲመሩ አዲስ ግደይ፣ ዳዋ ሁቴሳ፣ ሰመረ ሀፍተይ እና ብሩክ በየነ በእኩል 3ግቦች ተከታዩን ደረጃ ይዘዋል።
📷 ክሬዲት ፍቃዱ (ናታኒም ፊልም ፕሮዳክሽን)