የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን
ዋልያዎቹ ኬንያ ለምታስተናግደው
5ኛው የቻን የአፍሪካ ዋንጫ ውድድር
ለማለፍ ወሳኝ የሚባለውን የማጣሪያ
ጨዋታቸውን የፊታችን እሁድ በሐዋሳ
ኢንተርናሽናል ስታዲየም ከሱዳን
ብሔራዊ ቡድን ጋር ያደርጋሉ፤
ለእዚህም ጨዋታ ዝግጅታቸውን
በአዳማ ከተማ በመቀመጥ ሲለማመዱ
የቆዩ ሲሆን ከትናንት አንስቶ ደግሞ
ወደ ሐዋሳ ከተማም በማምራት
ዳግመኛ ዝግጅታቸውን እያጧጧፉት
ይገኛል፡፡
ዋልያዎቹ የቻን የአፍሪካ ዋንጫ
የማለፍ ህልማቸውን ለማሳካት
ለሚያደርጉት የእዚህ ጨዋታም
አቋማቸውን ለመፈተሽ ከዛምቢያ
ብሔራዊ ቡድን ጋር ቅዳሜ ዕለት
ሉሳካ ላይ የወዳጅነት ጨዋታቸውን
ያደረጉ ሲሆን በውጤቱም 0ለ0 ሊለያዩ
ችለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን
ተጨዋቾች የዛምቢያ አቻቸውን
በአቋም መለኪያው ግጥሚያ ሊፋለሙ
በመቻላቸውም ለዋናው የእሁድ
ጨዋታ በሚገባ እንደሚጠቅማቸውም
ሊናገሩ ችለዋል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ
ቡድን የሱዳን አቻውን የፊታችን እሁድ
ለሚፋለምበት ጨዋታም ግጥሚያውን
የሚመሩት ዳኞች ከወዲሁ የታወቁ ሲሆን
ዳኞቹም ከኡጋንዳ እንደሆኑም ታውቋል፤
ሁለቱ ሀገራት በሚያደርጉት የእዚህ የደርሶ
መልስ ጨዋታም አሸናፊው ሀገር በቀጥታ
ለኬንያው የቻን የአፍሪካ ዋንጫ ውድድር
የሚያልፍ ይሆናል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድንና የሱዳን
ብሄራዊ ቡድን ለወሳኙ የእሁድ ጨዋታ
ማለፋቸውን ያረጋገጡት የኢትዮጵያ ብሄራዊ
ቡድን የጅቡቲ አቻውን በመጀመሪያው
ግጥሚያ 5ለ1 ረትቶና የመልሱንም
የሐዋሳ ስቴድየም ጨዋታውን ጅቡቲዎች
ባለመምጣታቸው በፎርፌ በማሸነፍ ሲሆን
የሱዳን ብሄራዊ ቡድን ደግሞ ከብሩንዲ
ብሄራዊ ቡድን ጋር ያደረገውን ጨዋታ
በአጠቃላይ የደርሰ መልስ ውጤት 1ለ0
በማሸነፍ ሊያልፍ ችሏል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የሱዳን
አቻውን አሸንፎ ለኬንያው የቻን የአፍሪካ
ዋንጫ ማለፍ ከቻለ በውድድሩ ታሪክ
ለሶስተኛ ጊዜ በተከታታይ ማለፍ ከቻሉ
ጥቂት አገራት መካከል ስሙ የሚጠቀስ
ሲሆን ይህንንም ለማሳካት የቡድኑ
ተጨዋቾች በሚገባ እንደተዘጋጁም እየተነገረ
ይገኛል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ለእሁዱ
ወሳኝ ጨዋታ ከዛምቢያ ከተመለሰ በኋላ
ዝግጅቱን እያደረገ ባለበት የአሁን ሰዓት
በቅርቡ የብሔራዊ ቡድኑን እንዲቀላቀል
ጥሪ የደረሰው አዲሱ የቅዱስ ጊዮርጊስ
ፈራሚ ታደለ መንገሻም ስኳዱን በመቀላቀል
እየተለማመደ ይገኛል፡፡ ታደለ መንገሻ ቀደም
ሲል ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ተመርጦ
የነበረ ተጨዋች ሲሆን በጉዳት ሳቢያ ከቡድኑ
ውጪ ሆኖ እንደነበር ይታወቃል፤ ተጨዋቹ
የአሁን ሰዓት ላይ ዋልያዎቹን በመቀላቀሉም
ጥሩ የሆነ ስሜት እንደተሰማውም ተናግሯል፡
፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ሱዳንን እሁድ
በሚፋለምበት ጨዋታ የቡድኑ ተጨዋቾች
ግጥሚያውን አሸንፈው እንደሚወጡ
እየተናገሩ ሲሆን በደርሶ መልሱ ግጥሚያም
ለቻን የአፍሪካ ዋንጫ እንደሚያልፉም
እየተናገሩ ይገኛል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድንን ዝግጅት፤
ስለሚያደርጉት ግጥሚያና ተያያዥ በሆኑ
ጥያቄዎች ዙሪያ ከዋልያዎቹ ተከላካይ
አስቻለው ታመነ ጋር ቆይታ ያደረግን ሲሆን
ተጨዋቹም የሚከተለውን ምላሽ ሰጥቷል፡፡
ሀትሪክ፡- የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን
የሱዳን አቻውን እሁድ ይፋለማል፤
እያደረጋችሁ ያላችሁት ዝግጅት ምን
ይመስላል?
አስቻለው፡- የሱዳን አቻችንን
ለምንፋለምበት የእሁድ ጨዋታ እያደረግን
ያለነው ዝግጅት ምንም እንኳን ጊዜው አጭር
ቢሆንም ጥሩ የሚባል ነው፤ ከዝግጅታችን
ባሻገር የአቋም መለኪያ ግጥሚያንም ከዛምቢያ
ብሔራዊ ቡድን ጋር አድርገን አቋማችንን
በሚገባ ፈትሸናል፤ ከእነሱ ጋር ያደረግነው
ጨዋታም እሁድ ለምናደርገው ፍልሚያም
በበቂ ሁኔታ እንድንቀርብም ያስችለናል፡፡
ሀትሪክ፡- ከዛምቢያ ብሔራዊ ቡድን ጋር
ስላደረጋችሁት የአቋም መለኪያ ጨዋታ ምን
ትላለህ?
አስቻለው፡- ዛምቢያን የገጠምንበት
የወዳጅነት ጨዋታ ለእኛ ጥሩ የሚባል
ነበር፤ በመጀመሪያው አጋማሽ የእነሱን
አጨዋወት ለማጥናት በሚል ወደኋላ
በማፈግፈግና ኳስን በመቆጣጠር ጭምርም
በጥንቃቄ መልኩ ተጫውተናል፡፡ በእዚሁ
እንቅስቃሴ ውስጥ ሆነንም በተለይ እነሱ
በመስመር በኩል ተጭነውን ለመጫወት
የሞከሩበትን እንቅስቃሴ ኳስን ይዘን
ለመጫወት በመቻል ልንገድባቸው ችለናል፤
ስኬታማ እንዳይሆኑም አድርገናል፡፡
የሁለተኛው አጋማሽ ላይም የእኛ ቡድን
እንደመጀመሪያው አጋማሽ ሙሉ ለሙሉ
ባይሆንም ጥሩ ለመጫወት የሞከረበት
አጋጣሚን ልንመለከትበት ችለናል፤
ግጥሚያውን በአቻ ውጤትም ልናጠናቅቅ
ችለናል፡፡
ሀትሪክ፡- ከዛምቢያ ጋር በነበራችሁ
ጨዋታ ያጋጠመህ የተለየ ነገር አለ?
አስቻለው፡- አዎን፤ የቅዳሜው
የአቋም መለኪያ ጨዋታችን ላይ የእነሱ
ደጋፊዎች ቡድናቸውን ይቃወሙ ነበር፤
የሚቃወሙትም አሰልጣኙን ነው፤ እኛ
ኳስን ይዘን በምንጫወትበት ወቅት ደግሞ
ድጋፋቸውን በጭብጨባ ይገልፁልን ነበርና
ያንን ነው ለመመልከት የቻልኩት፡፡
ሀትሪክ፡- የሱዳን ብሔራዊ ቡድን
ጋር በሚኖራችሁ የእሁዱ ወሳኝ ጨዋታ
ከግጥሚያው ምን ውጤት ትጠብቃለህ?
ስለተጋጣሚያችሁስ ወቅታዊ አቋምስ ምን
የምታውቁት ነገር አለ…
አስቻለው፡- ከሱዳን ብሔራዊ ቡድን
ጋር ለሚኖረን የእሁድ ጨዋታ የአሁን
ሰዓት ላይ እያደረግን ያለነው ዝግጅት
ጥሩ የሚባል ነው፤ ስለተጋጣሚያችን
ሱዳን ወቅታዊ አቋም በተመለከተ በቅርቡ
ከምንመለከተው ጨዋታ በመነሳት ልናውቅ
የምንችልበት እድሉ ቢኖረንም ስለእነሱ
ጠንካራነት በሚገባም እናውቃለን፡፡ ሱዳኖች
በክለብና በብሄራዊ ቡድን ደረጃም ትልቅ
ከሚባሉ አገራት መካከልም ስማቸው
የሚጠቀስ ነውና ከእነሱ ጋር የሚኖረንን
ጨዋታ ለማሸነፍ ነው ወደ ሜዳ የምንገባው፤
የግጥሚያውን ውጤትም እዚሁ ጨርሰን
ለመሄድም ነው እየተዘጋጀን ያለነው፡፡
ሀትሪክ፡- ከሱዳን ጋር በሚኖረው የቻን
የአፍሪካ ዋንጫ የደርሶ መልስ ጨዋታ
የማለፍ ህልማችሁ ይሳካል?
አስቻለው፡- አዎን፤ ለማለፍም እኮ ነው
እየተጫወትን ያለነው፤ ዋናው ግጥሚያ
የእሁዱ ነው በጥሩ የጎል ልዩነቶችም
በማሸነፍ ነው የቻኑ የአፍሪካ ዋንጫ የማለፍ
ተስፋችንን በእርግጠኝነት የምናሳከው፡፡
ሀትሪክ፡- የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን
ላይ ያየኸው ጠንካራ እና ደካማ ጎን
ምንድነው?
አስቻለው፡- የዋልያዎቹ ስብስብ ላይ
የተመለከትኩት ጠንካራ ጎን ቡድኑ ልምድ
ያላቸውንና ለመጀመሪያ ጊዜም የተመረጡ
ተጨዋቾችን ይዞ በጥሩ ፍቅር፣ ህብረትና
መከባበርም የተገነባ መሆኑ ነው፤ እንደ
ክፍተት ያየሁት ብዙ ነገር ባይኖርም
በተወሰነ መልኩ ያየሁት ግን ስኳዱ
አዲስ ከመሆኑ አኳያ በተወሰነ መልኩ
አለመቀናጀታችንን ነው፡፡
“ሱዳንን በማሸነፍ የቻን የአፍሪካ ዋንጫ የማለፍ ህልማችንን እናሳካለን” አስቻለው ታመነ
Managing Editor at Hatricksport Website