መቐለ 70 እንደርታ በሁለት ደቂቃዎች ልዩነት ባስቆጠርዋቸው ሁለት ግቦች ታግዘው የ2012 ፕሪምየር ሊግን በአሸናፊነት ጀመረዋል።በዝግ ስታድየም በተካሄደው ጨዋታ መቐለ 70 እንደርታዎች በአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ ፋሲልን ከገጠመው ስብስብ አሌክስ ተሰማን በላውረንስ ኤድዋርድ ሲቀይሩ አዲስ አዳጊዎቹ ሀድያዎች በበኩላቸው በርካታ አዳዲስ ፈራሚዎቻቸውን ቀዋሚ 11 ውስጥ አካተው ጨዋታውን ጀምረዋል።
የመቐለ 70 እንደርታ በአንፃራዊነት የተሻለ የኳስ ቁጥጥር ብልጫ በታየበት የመጀመርያ አጋማሽ ሻምፒዮኖቹ የሀድያ ሆሳእና ጠጣር መከላከልን ሰብሮ መግባት ከብድዋቸው ታይቷል።በተለይ ኳሱ የሜዳው መጨረሻ ክፍል በሚደርስበት ጊዜ በቀላሉ በሀድያ ሆሳእና ተጨዋቾች ሲጨናገፍባቸው ነበር፤በዚህም ምክንያት ከመስመር የሚነሱ ኳሶችን በመጠቀም የግብ እድሎችን መፍጠር ምርጫቸውን አድርገዋል።በተለይ አሸናፊ ሃፍቱ አሻምቶት ያሬድ ከበደ በግምባሩ የመታው ኳስ ታሪኬ ጌትነት ወደ ውጭ አውጥቶበታል።በተጨማሪ አማኑኤል ገብረሚካኤል ከሳሙኤል ሳሊሶ የተላከለትን ኳስ ከታሪኬ አናት አሳልፎ ለማስቆጠር ቢሞክርም ኳሱ ወደ ውጭ ወጥቶበታል።ሀድያዎች በበኩላቸው አብዛኛው ጊዜያቸውን መከላከል ላይ ትኩረት ቢያደርጉም ከቆሙ ኳሶች የግብ እድሎችን መፍጠር ችለዋል።አፎርቅ ሀይሉ ከማእዘን ምት አሻምቶት ፊሊፕ ኦቮኖ መልሶት የተገኘውን ኳስ እዮብ በቃቱ መልሶ ቢመታውም ኦቮኖ በድንቅ ብቃት መልሶ አድኖበታል።ባለሜዳዎቹ መቐለ 70 እንደርታዎች በመጀመርያው አጋማሽ የመጨረሻ ደቂቃ ላይ በአስናቀ ሞገስ አማካኝነት ያደረግው ሙከራ ታሪኬ ጌትነት ሊያድንበት ችሏል።በዚህም መሰረት የመጀመርያው አጋማሽ ግብ ሳይቆጠርበት ተጠናቋል።
- ማሰታውቂያ -
በቢስማርክ አፖንግ ቀላል ሙከራ የተጀመረው ሁለተኛው አጋማሽ ሁለቱም ቡድኖች የተሻለ መንቀሳቀስ የቻሉበት ነበር።በተለይ መቐለዎች በሁለተኛው አጋማሽ ጥሩ መናበብ በነበራቸው አማኑኤል እና ያሬድ ከበደ ጥምረት በመጠቀም በ54ኛው ደቂቃ መሪ ያደረጋቸውን ግብ አግኝተዋል።አማኑኤል ከግራ መስመር መሬት ለመሬት ያሻማው ኳስ ያሬድ ከበደ ሁለት ተጨዋቾችን በመቀነስ መቐለን መሪ አድርጓል።የመጀመርያው ግብ ከተቆጠረ ከአንድ ደቂቃ በኃላ ከመሀል ሜዳ በቀጥታ ወደ አማኑኤል ገብረሚካኤል የተላከ ረጅም ኳስ አማኑኤል የሚታወቅበትን ፍጥነቱን በመጠቀም ከሁለት ተከላካዮች መሀል አፈትልኮ በመውጣት በጥሩ አጨራረስ የሻምፒዮኖቹን መሪነት ወደ ሁለት ከፍ አድርጓል።ከሁለተኛው ግብ በኃላ መነቃቃት ያሳዩት ሀድያዎች በ59ኛው ደቂቃ ያገኙትን ማእዘን ምት በደስታ ዲቻሞ አማካኝነት አስቆጥረው ወደ ጨዋታው መመለስ ችለዋል።ከግቡ በኃላ መነቃቃት ያሳዩት ሀድያዎች ተከላካያቸውን በረከት ወልደዮውሃንስን በአጥቂው ሙሳ ካማራ በመቀየር የመቐለ ተከላካይ ክፍልን ለመስበር ቢሞክሩም የጠራ የግብ እድል መፍጠር ሳይችሉ ጨዋታው በመቐለ 70 እንደርታ አሸናፊነት አጠናቋል።
የአሰልጣኞች አስተያየት
አስልጣኝ ገብረመድህን ኃይሌ በሰጡት አስተያየት “ማሸነፋችን ጥሩ ቢሆንም ብዙ እንቅስቃሴ ያላሳየንበት ምክንያት ያለተመልካች በዝግ ስታዲዮም በመጫወታችን ጥሩ እንቅስቃሴ አላሳየንም” ብለዋል ።
በቀጣይ ውድድር በቅጣትና በጤና ምክንያት የተጓደሉ ተጫዋች አሟልተው ጥሩ ውጤት ለማምጣት እንደሚዘጋጁ ተናግረዋል።
የሃዲያ ሆሳእና አሰልጣኝ ኢዘዲን አብደላ በበኩላቸው “በዝግ ስታዲየም በመጫወታችን ፉክክራችን ቀዝቃዛ ቢሆንም ቆንጆ ተጫውተናል፤ ያገኘነው ውጤት ሽንፈት ቢሆንም በቀጣይ ጉድሎቶቻችንን አስተካክለን ጥሩ ተፎካካሪ እንሆናለን “ ሲሉ ገልጸዋል።