በኢትየጵያ ፕሪምየር ሊግ የሶስተኛ ሳምንት ጨዋታ ዛሬ(እሁድ) ተደርጎ ደደቢት ባለድል መሆን ችሏል። 9:05 ሲል የተጀመረው የደደቢት እና ሀዋሳ ከተማ ጨዋታ በደደቢት 2-1 አሸናፊነት ተጠናቋል።
10ኛው ደቂቃ ላይ የደደቢቱ አጥቂ ጌታነህ ከበደ ፍፁም ቅጣት ምት ክልል ውስጥ አግኝቶ የሞከረው ኳስ በግቡ አናት ላይ ወጥቷል። ከ1 ደቂቃ በኋላ የሀዋሳ ከተማው ዳዊት ፍቃዱ የመታው ኳስ የግቡን ቋሚ ለትሞ ተመልሷል። ኳስ ካቆመ በኀላ ተመልሶ መጫወት የጀመረው የቀድሞ የቅ/ጊዮርጊስ እና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ድንቅ አማካይ ሙሉዓለም ረጋሳ ድንቅ ሆኖ በዋለበት በዚህ ጨዋታ 13ኛው ደቂቃ ላይ የሀዋሳ ከተማው ታፈሰ ሰለሞን ከሳጥን ውጪ የመታውን ኳስ አስቆጥሮ ቡድኑን ቀዳሚ ማድረግ ችሎ ነበር። ከግቡ መቆጠር በኋላ ተጭነው የተጫወቱት ሀዋሳ ከተማዎች 25ኛው ደቂቃ ላይ የደደቢቱ ብርሀኑ ቦጋለ(ፋዲጋ) የሰራውን ስህተት ተጠቅሞ ዳዊት ፍቃዱ በረኛውን አልፎ የሞከራት ኳስ ወጥቶበታል።
28ኛው ደቂቃ ላይ በጨዋታው ጥሩ እንቅስቃሴ ያሳየው አቤል ያለው የመታውን ኳስ በረኛው ሲመልሰው አጠገቡ የነበረው የደደቢት አጥቂ ጌታነህ ከበደ አስቆጥሮ ቡድኑን አቻ ማድረግ ችሏል።
ከመጀመሪያው አጋማሽ ተሽለው ወደ ሜዳ የገቡት ደደቢቶች ሁለተኛውን ግብ ለማስቆጠር 6ደቂቃ ብቻ ነበር የወሰደባቸው። 51ኛው ደቂቃ ላይ አቤል ያለው ከቀኝ ክንፍ በኩል ያገኘውን ኳስ በግሩም ሁኔታ ወደ ግብነት ቀይሯታል። ከ3 ደቂቃዎች በኋላ ጌታነህ የሞከረውን ኳስ የሀዋሳ ግብ ጠባቂ በድንቅ ሁኔታ አውጥቶበታል።
ከመጀመሪያው አጋማሽ ይልቅ በሁለተኛው አጋማሽ እጅግ ተዳክመው ወደ ሜዳ የገቡት ሀዋሳ ከተማዎች 61ኛው ደቂቃ ላይ በፍሬው ሰለሞን በጭንቅላት ኳስ ቢሞክርም ኳሱ በግቡ አናት ላይ ወጥቷል። ከዚህ በኋላም ይሄ ነው የማይባል ሙከራ ሳይደረግ ጨዋታው በደደቢት አሸናፊነት ተጠናቋል።
ከጨዋታው መጠናቀቅ በኋላ የሁለቱም ቡድን አሰልጣኞች አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
የደደቢት አሰልጣኝ ንጉሴ ደስታ “ወደ አሸናፊነት በመምጣታችን በጣም ደስ ብሎኛል። ልጆቹ ያደረጉትን ጥረት አደንቃለሁ፤ ከዚህም በላይ ግን መሻሻል እንዳለብን አስባለሁ። ከጨዋታ ጨዋታ እየተሻሻልን በመሄድ ለዋንጫ ፉክክር የምናደርገውን ጥረት እንቀጥላለን።” በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
የሀዋሳ ከተማው አሰልጣኝ ውበቱ አባተ በበኩላቸው “ጨዋታውን ለመቆጣጠር ጥረት አድርገናል፤ እንደ ቡድን መጫወት ላይ መጥፎ አልነበርንም። መከላከል ላይ የራሳችን ክፍተት ነበረብን፤ እነሱም ዋጋ አስከፍለውናል። ጨዋታው ላይ ግልፅ የዳኝነት ችግር አስተውለንበታል። ይህም ሊታረም ይገባል።” በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።