በዘንድሮው የኢትዮጵያ ኘሪሚዬር ሊግ ጥሩ ያልሆነ የውድድር ጊዜ በማሳለፍ ላይ የሚገኙት አርባምንጭ ከተማዎች ከ3 ወራት በፊት አሰልጣኝ ፀጋዬ ኪ/ማርያምን አሰናብተው በምትካቸው የሾሟቸውን አሰልጣኝ እዮብ ማለን ዛሬ ከክለቡ ማሰናበታቸው ቢነገርም አሰልጣኝ እዮብ ማለ በበኩላቸው ከክለቡ ስለመሰናበቴ በይፋ የደረሰኝም ሆነ የተነገረኝ ነገር የለም ብለዋል፡፡አርባምንጭ ከተማዎች በ21ጨዋታዎች በ19 ነጥብ በደረጃ ሰንጠረዡ 14ኛ ላይ ተቀምጠው የመውረድ ስጋት ውስጥ ገብተዋል፡፡
አሰልጣኝ እዮብ ማለ (አሞካቺ) ከአዞዎቹን ጋር በነበራቸው የ3 ወራት ቆይታ 11 የኘሪሚዬር ሊግ እና 1 የኢትዮጵያ ዋንጫ የጥሎ ማለፍ ጨዋታ ላይ ቡድኑን የመሩ ሲሆን ፡በ4 ጨዋታ ሲያሸንፉ፡በ2ጨዋታ አቻ እና በ5 ጨዋታ ሽንፈት ሲያስተናግዱ በኢትዮጵያ ዋንጫ የጥሎ ማለፍ የመጀመሪያ ጨዋታ ከሜዳቸው ውጭ 1ጨዋታ አሸንፈዋል፡፡
አሰልጣኝ እዮብ ማለ ለሀትሪክ ስፓርት ድህረገጽ እንደገለፁት ከክለቡ ስለመሰናበቴ እስካሁን በይፋ የተነገረኝም ሆነ የደረሰኝ ነገር የለም ፡፡መረጃው እንደማንኛውም ሰው ደርሶኛል፡፡ከክለቡ ጋር በነበረኝ ቆይታ ግን ያን ያህል መጥፎ ውጤት አላስመዘገብኩም ነበር በማለት አክለውም ከአዞዎቹ ጋር እስከ ሰኔ 2010ዓ/ም የሚያቆይ ኮንትራት ውል እንዳላቸውም ነግረውናል፡፡