በበርካታ የሶዶ አካባቢ ስፖርት አፍቃሪ በሜዳ ላይ በመገኘት የተከታተለው የኢትዮጵያ ኘሪሜየር ሊግ 17ኛ ሳምንት ጨዋታ በአፍሪካ ኮንፌዴሬሽን ካፕ ሀገርን ወክሎ እየተሳተፈ እሚገኘው ወላይታ ድቻ ሁለተኛውን ዙር በአዲሱ አሰልጣኝ ስዩም ከበደ እየተመራ ከገባው መከላከያ ጋር ነጥብ ተጋርተው ወጥተዋል።
በሶዶ ሁለገብ ስታዲየም ልክ 9 ሰዓት ሲል የተጀመረው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በመጀመሪያው አርባአምስት የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ኳስን አደራጅቶ ፣በመከላክሉ ረገድ እንዲሁም የመሃል የሜዳ ክፍል ብልጫ ከባለሜዳው ወላይታ ድቻዎች በመውሰድና ወደ ተቃራኒዉ ቡድን የግብ ክልል በመድረስም መከላከያ የተሻለ ነበር፡፡
ባለሜዳዎች ወላይታ ድቻዎች ኳስን መሠረት አድርገው ፍሰት ያለው ኳስ በመልሶ ማጥቃት እንቅስቃሴ ቢያደርጉም ግብ ማስቆጠር አልቻሉም፡፡
በዚሁ የመጀመሪያው አጋማሽ ተጠናቆ ወደ መልበሻ ቤት አምርተዋል።
ከዕረፍት መልስ እንግዳዎ መከላከያ ቶሎ ቶሎ ወደተቃራኒው የግብ ክልል በመድረስ የተሻሉ ነበር። በተለይም ከእረፍት መልስ በ67ኛው ደቂቃ ላይ በሊጉ 6ያኽል ግቦችን ያስቆጠረው ምንይሉ ወንድሙ ከመስመር የተሻገረለትን ኳስ በጭንቅላቱ የሞከረው ኳስ የወላይታ ድቻው ግብ ጠባቂ ወንደሰን ገረመው (ፓንቼ) በድንቅ ሁኔታ ግብ ከመሆን አክሽፏታል፡፡
- ማሰታውቂያ -
ከ70ኛ ደቂቃ በኃላ ወላይታ ድቻዎች በአንጻሩ በመሃል ሜዳ የተወሰደባቸውን ብልጫ ለመመለስ ፈጣን እንቅስቃሴ በመምረጥና ወደጎል በመድረስ ተጭነው ለመጫወት ሲሞክሩ ተስተውሏል፡፡
ደቂቃዎች እየገፉ በመጡ ቁጥር ሁለቱም ክለቦች ጥንቃቄን የተላበሰ እንቅስቃሴ በመምረጣቸው ጨዋታው ያለ ግብ 0-0 በሆነ አቻ ውጤት ሊጠናቀቅ ችሏል።
የአሰልጣኞች አስተያየት
አሰልጣኝ ዘነበ ፍስሀ – ወላይታ ድቻ
“በጨዋታው በሜዳ ለመተግበር ተነጋግረን የገባነውን የጨዋታ ስትራቴጂ ተጨዋቾቼ ተግባራዊ ባለማድረጋቸውና መከላከል ላይ በማተኮራቸው ነጥብ ተጋርተን ለመውጣት ተገደናል። “
አሰልጣኝ ስዩም ከበደ-መከላከያ
“በዛሬው ጨዋታ ከሜዳችን ውጭ እንደመጫወታችን ነጥብ ይዘን ለመመለስ አቅደን ነበር፤ የገባነው ይህንንም አሳክተናል። በውጤቱ ደስተኛ ነኝ “