በአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳታፊ የነበረው ቅ/ጊዮርጊስ ወደ ካምፓላ ተጉዞ በኡጋንዳው ኬሲሲኤ 1-0 ተሸንፎ ከውድድሩ ውጪ መሆን ችሏል።
ቅ/ጊዮርጊስ በተለመደው የ4-3-3 የጨዋታ ዘይቤ ወደሜዳ ሲገቡ ኬሲሲኤዎች በአንፃሩ በ3-5-2 የጨዋታ ዘይቤ ወደ ሜዳ ገብተዋል። ባለሜዳዎቹ ኬሲሲዎች በጨዋታው የመጀመሪያ ደቂቃዎች ጎል ለማግኘት ጫና ፈጥረው የተጫወቱ ሲሆን የመጀመሪያውን የግብ ሙከራ ማድረግ የቻሉት ግን ቅ/ጊዮርጊሶች ነበሩ። 4ኛው ደቂቃ ላይ የቅ/ጊዮርጊሱ አብዱልከሪም ኒኪማ ወደ ጎል የሞከረውን ኳስ የኬሲሲኤው ግብ ጠባቂ ይዞበታል።8ኛው ደቂቃ ላይ የኬሲሲው አማካይ ሙኩሪዚ ፓውል በጥሩ ሁኔታ የመታውን ኳስ የቅ/ጊዮርጊሱ ግብ ጠባቂ ሮበርት ኦዶንካራ በጥሩ ሁኔታ መልሶታል። የቅ/ጊዮርጊሱ ግብ ጠባቂ ሮበርት ኦዶንካራ በዛሬው ጨዋታ ፍፁም ድንቅ ብቃቱን ያሳየ ሲሆን በተደጋጋሚ ጊዜ የሚሞከሩበትን ከባባድ የግብ ማግባት ሙከራዎችን ሲያመክን ውሏል። 20ኛው ደቂቃ ላይ ኬሲሲኤዎች ጥሩ ኳስ ወደ ጎል ይዘው ገብተው ሮበርት በድጋሚ በድንቅ ብቃት ኳሱን መልሶበታል።
በቀሪው የመጀመሪያ አጋማሽ ጨዋታ ቅ/ጊዮርጊስ ወደኋላ በማፈግፈግ በመልሶ ማጥቃት ለመጫወት ጥረት ቢያደርጉም አቡበከር ሳኒ በተደጋጋሚ ያገኛቸውን ኳሶች መጠቀም ባለመቻሉ ቡድኑ ውጤት ሳይዝ ሊወጣ ችሏል። በዚህም የመጀመሪያው አጋማሽ ግብ ሳይስተናገድበት 0-0 ሊጠናቀቅ ችሏል።
በሁለተኛው አጋማሽ ሁለተኛ ደቂቃ ላይ ግብ ያስተናገደው ይህ ጨዋታ 47ኛው ደቂቃ ላይ የቅ/ጊዮርጊስ ግብ ጠባቂ እና ተከላካዮች የሰሩትን ስህተት ተከትሎ ያገኘውን ኳስ የኬሲሲኤው መሀመድ ሻባን አስቆጥሮ ቡድኑን ቀዳሚ ማድረግ ችሏል። ከዚህ ግብ መቆጠር በኋላም በሁለቱም ቡድኖች በኩል ግብ ለማስቆጠር ጥረት ያደረጉ ሲሆን በተለይ ፈረሰኞቹ በመልሶ ማጥቃት ወደ ተጋጣሚያቸው የግብ ክልል በተደጋጋሚ ቢደርሱም በኬሲሲኤ ተከላካዮች እና በግብ ጠባቂው ሉኩዋጎ ቻርለስ ድንቅ ብቃት ወደግብነት መቀየር ሳይችሉ ቀርተዋል።
በዚሁም ጨዋታው በባለሜዳዎቹ ኬሲሲኤ 1-0 አሸናፊነት ሊጠናቀቅ ችሏል። ከ10 ቀናት በፊት አ/አ ላይ በነበረው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ 0-0 የተለያዩ ሲሆን ይህንንም ተከትሎ ቅ/ጊዮርጊስ በድምር ውጤት 1-0 ተሸንፎ ከውድድሩ ውጪ ሲሆን ኬሲሲኤ በአንፃሩ በኡጋንዳ ክለቦች ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ምድብ ድልድል መግባት የቻለ ቀዳሚው ክለብ መሆን ችሏል።
- ማሰታውቂያ -
የፎቶ ምንጭ የኬሲሲኤ የፌስቡክ ገጽ