ጅማ አባቡናም ሆነ ሌሎች በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ተመዝግበው የሚገኙ ክለቦች በሚወዳደሩበት ሊግ ለ2010 ዓ.ም ውድድር ዝግጅት ከነሐሴ 1/2009 ጀምሮ እስከ ጥቅምት 5/2010 ዝግጅት እንዲያደርጉና እንዲመዘገቡ በቀን 24/12/09 በቁጥር 2/ኢ.አ.ፌ አ.9/143 በተፃፈ ደብዳቤ ተገልጾላቸዋል፡፡
ጅማ አባቡና “በኤሌክትሪክና በሀዋሳ ከተማ መካከል የተደረገው የመጨረሻ ጨዋታ ውጤት የማስለወጥ ተግባር ታይቶበታል” ፣ “ሀዋሳ ከተማ ከኤሌክትሪክ ክለብ ጋር ያደረገው ጨዋታ ሕገ ወጥ ነው” በማለት በመጠየቁ ምክንያት ብቻ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን በዕለቱ የተመዘገበውን ውጤት መለወጥ ስለሌለበት ለሁሉም ክለቦችና ለሚመለከታቸው አካላት የክለቦች ደረጃ በሰንጠረዥ ተሰርቶ የጅማ አባቡና ክለብ በ14ኛ ደረጃ ውድድሩን ማጠናቀቁን አሳውቀናል፡፡ በእጣ አወጣጥ ስነ-ስርአት ላይም ኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ የተገኘ ሲሆን ጅማ አባቡና በተመደበበት ሊግ ሳይገኝ ቀርቷል፡፡
ክለቡ “ደባ ተሰርቶብኛል” በማለት ያቀረበውን አቤቱታ በተመለከተ በየደረጃው የምንችለውን የማጣራት ሥራ አከናውነናል፡፡ ይሁንና በአንዳንድ መገናኛ ብዙሀን ግን ምንም እንዳልተሰራና ውሳኔ ያልተሰጠ ጉዳይ እንደሆነ እየተነገረ ይገኛል፡፡ ፍጹም ስህተት ነው፡፡ የውድድሩ ዘመን በተፈፀመ ማግስት የሁሉም ተወዳዳሪ ክለቦች ውጤት ተገልጾአል፡፡ የሀዋሳ ከተማና የኤሌክትሪክ ክለቦች ውጤት በተላከላቸው ኮሚኒኬ አማካኝነት አውቀውታል፡፡ የጅማ አባቡና ክለብ ምንም እንዳልደረሰው ወይም እንደማያውቅ ተደርጐ መገለፁ ትክክል ሆኖ አላገኘውም፡፡ አንዳንድ የመገናኛ ብዙሀን ሙያተኞች የተሰራው ሥራ ተስኖአቸው ሳይሆን የራሳቸው በሆኑ አንዳንድ ምክንያቶች ትክክለኛውን እውነታ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ለመግለፅ አለመፈለጋቸው የፈጠረው ችግር እንደሆነ ግልፅ ነው፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የጅማ አባቡናን አቤቱታም በጥልቀት የተመለከተው ሲሆን ከሚመለከታቸው የክለቡ ኃላፊዎችና ከባለድርሻ አካላት ጋር በጉዳዩ ዙሪያ በተደጋጋሚ ተወያይቶአል፡፡ በዚሁ መሠረት በፌዴሬሽኑ በኩል የሚከተሉት ዕርምጃዎች ተወስደዋል፡-
1ኛ. የጅማ አባቡና እግር ኳስ ክለብ ከጨዋታ ውጤት ማስለወጥ ጋር ተያይዞ ላቀረበው ጥያቄ ማስረጃ እንዲያቀርብ በቁጥር 2/ኢ.እ.ፌ.አ-9/1280 በቀን 14/10/2009 ዓ.ም በተጻፈ ደብዳቤ ተጠይቋል፤
2ኛ. የደቡብ ክልል ፖሊስ ኮሚሽንና የሀዋሳ ከተማ እግር ኳስ ክለብ ማስረጃዎችን እንዲልኩ ለሁለቱም ተቋማት በቁጥር 2/ኢ.እ.ፌ-አ.9/1328 በቀን ሐምሌ 26/10/2009 ዓ.ም በተፃፈ ደብዳቤ ጠይቀናል፤
3ኛ. ኢትዮ ቴሌኮም ማስረጃዎችን እንዲልክ በ20/11/2009 እና 17/12/09 በተፃፉ ደብዳቤዎች ጥያቄ ቀርቧል፤
4ኛ. አጣሪ ኮሚቴ በመሰየም የማጣራት ስራ እንዲከናወን ተደርጓል፣ ሪፖርት ተጠናቅሮና ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጥቷል፤
5ኛ. ማስረጃዎችን በማሰባሰብና በማደራጀትም ጉዳዩ በዲሲኘሊን ኮሚቴ እንዲታይ አስፈላጊው መመሪያ ተሰጥቷል፤
6ኛ. ለጅማ አባቡና እና ለሚመለከታቸው አካላት ፌዴሬሽኑ አቤቱታውን በአግባቡ እየመረመረ ስለመሆኑ በጹሁፍና በስልክ ተደጋጋሚ መረጃ ተሰጥቷል፤
7ኛ. የዲሲኘሊን ኮሚቴ በ22/12/09 ዓ.ም ያቀረበውን የውሳኔ ሃሳብ መሰረት በማድረግም 29 ገፅ ሰነዶችና አንድ ሲዲ ለፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን በቀን 23/12/09 ዓ.ም እንዲላክ ተደርጓል፤
8ኛ ጉዳዩ ወደ ፌዴራል ወንጀል ምርመራ ቢሮ መላኩን ተከትሎም ተከታታይ ክትትል ከማድረግ በተጨማሪ የኮሚሽነሮችና ዳኖች ሪፖርቶች እና ሌሎች የጹሁፍ ማስረጃዎተን ጨምሮ 12 ምስክሮች በአካል ቀርበው ቃላቸውን እንዲሰጡ ተገቢውን ክትትልና ጥረት አድርጓል፣
9ኛ. የፖሊስ ምርመራ መጠናቀቁን ተከትሎም መዝገቡ በ24/01/10 ለአቃቢ ህግ የተላከ ሲሆን የፍትህ አካል የሚሰጠውን ውሳኔ ፌዴሬሽኑ በመጠባበቅ ላይ ይገኛል፡፡
እንደሚታወቀው ማንኛውም ሰው ወንጀልም ሆነ የሚያስጠይቅ ጥፋት ሰርቶ ሲገኝ በሀገሪቱ ሕግ መሰረት የሚዳኝ ስለሆነ በእኛ በኩል ያሰባሰብነውን መነሻ የሚሆኑ ሰነዶች ለፍትህ አካላት ሰጥተናል፣ የሚሰጡት ውሳኔዎች የሚያስጠይቁ ሆነው ከተገኙ የእግር ኳስ ፌዴሬሽን በደንቡ መሠረት ዕርምጃ ይወስዳል፡፡ ይሁን እንጂ ከላይ በተገለፀው መሰረት የሀዋሳ ከተማ እና የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ የዕለቱ ውጤት ቀደም ሲል የፀደቀ መሆኑን እያስታወስን በፌዴሬሽኑ በኩል የዘገየ ውሳኔ አለመኖሩን እንገልፃለን፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሸን»