የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን የ2009 በጀት ዓመት ጠቅላላ ጉባኤውን የመጀመሪያ ቀን ውሎ ዛሬ(ጥቅምት 30) አከናወነ። በኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል በተደረገው እና ከተመረጡ ሚዲያዎች ውጪ አላስገባም በማለቱ ከጋዜጠኞች ጋር አላስፈላጊ ጭቅጭቅ እና ንትርክ ውስጥ ገብቶ ይጀመራል ከተባለበት 2 ሰዓት አርፍዶ የጀመረው ጉባኤው በርካታ መወያያ ሀሳቦች ተነስተው ተሰብሳቢዎቹም ተወያይተውባቸዋል።
ምልዐተ ጉባኤው እንደተሟላ ለማረጋገጥ በተደረገው ቆጠራ በጉባኤው ከሚሳተፉ 142 አባላት 126 በመገኘታቸው ጉባኤው ተጀምሯል። ከዚህም በኀላ በቀረቡት አጀንዳዎች ላይ ውይይት የተደረገ ሲሆን ጉባኤተኞቹን ለሁለት የከፈለ ነገር ተከስቷል። አንደኛው ወገን ህጉ ስላልተከበረ ምርጫው መራዘም አለበት ሲል ሌላኛው ወገን ደግሞ የተፈጠረ አዲስ ነገር ስለሌለ አጀንዳ የሚያስቀይረን ምንም ነገር የለም በማለት ሀሳባቸውን አንፀባርቀዋል። ከዚህም ውይይት በኀላ ጥያቄው (ይራዘም ወይም አይራዘም) በድምፅ ብልጫ እንዲወሰን ተደርጎ ከተሰብሳቢዎቹ መካከል 68ቱ ይራዘም ሲሉ 62ቱ ደግሞ አይራዘም ብለዋል። በዚህም መሰረት በ 68 ድጋፍ በ 62 ተቃውሞ እና በ 12 ድምፀ ተአቅቦ ምርጫው ላልተወሰነ ጊዜ ተራዝሟል። ከዚህም ጋር ተያይዘው የተነሱ ሀሳቦች ነበሩ። ከነዛም መካከል አሁን ያለው ስራ አስፈፃሚ ሆነ ፕሬዝደንት የስልጣን ጊዜያቸውን ስለጨረሱ ምርጫው እስከሚካሄድበት ቀን ድረስ ጊዜያዊ ስራ አስፈፃሚ እና ፕሬዝደንት ይመረጥ የሚል ሀሳብ ሲነሳ በሌላ በኩል ደግሞ የአፋር እግር ኳስ ፌደሬሽን ተወካይ ጠቅላላ ጉባኤው ከአፋር ወደ አ/አ የተዛወረበት ምክንያት ግልፅ ስላልሆነ ማብራሪያ ቢሰጥ ሲሉ የቅ/ጊዮርጊሱ ተወካይ ምርጫው አፋር እንዲደረግ እንፈልጋለን ብለዋል። የደደቢት ተወካይም የቅ/ጊዮርጊሱ ተወካይ ያነሱትን ሀሳብ በመደገፍ አስመራጭ ኮሚቴ ይቋቋም የሚል ሀሳብም አቅርበዋል።
ከምሳ መልስ ከተሳታፊዎች የተለያዩ ጥያቄዎች ተነስተው ከስራ አስፈፃሚዎቹ ምላሽ ተሰጥቶበታል። ከተነሱት ጥያቄዎች ዋና ዋናዎቹ
ስለ ስፖርታዊ ጨዋነት በቂ ነገር ተሰርቷል ብለው እንደማያምኑ፣ የተጫዋቾች ዝውውር መመሪያም ወጥቶ ነበር አፈፃፀሙ ግን ክፍተት እንዳለው፣ 18.4 ሚሊየን ብር ከስቴዲየም ገቢ ተገኝቷል የተባለው ከብሄራዊ ቡድኑ ነው ወይስ ከክለቦች? እንዲሁም ስለሚፈርሱት ክለቦች ጥያቄ ተነስቶ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና የዳሽን ቢራ ተወካዮች ሀሳባቸውን አንፀባርቀዋል። ዳሽን የፈረሰው በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ኢ-ፍትሃዊ አሰራር ነው ሲሉም የዳሽን ቢራ ተወካይ ጨምረው ተናግረዋል። ለነዚህና ለሌሎች ከቤቱ ለተነሱ ጥያቄዎች የፌደሬሽኑ ፕሬዝደንት አቶ ጁነዲን ባሻ፣ እንዲሁም አቶ ተክለወይኒ አሰፋ እና አቶ አበበ ገላጋይ ምላሽ ሰጥተውባቸዋል።
ከክለቦቹ ተወካዮች የሊግ ኮሚቴ ስለማቋቋም ለተነሳላቸው ጥያቄ አቶ ጁነዲን ባሻ ሲመልሱ መጀመሪያ ክለቦቹ አንድ መሆን እና ዝግጁ መሆን አለባቸው ሲሉ በአፅንኦት ተናግረዋል።
ጠቅላላ ጉባኤው ነገ በሁለተኛ ቀኑ ሲቀጥል የምርጫው ጊዜ መቼ ይሁን ለሚለው፣ ስለ አስመራጭ ኮሚቴ፣ ስለ ጊዜያዊ ስራ አስፈፃሚ እና ሌሎች ሀሳቦች ላይ ይወያያል ተብሎ ይጠበቃል።
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ጠቅላላ ጉባኤውን ዛሬ ጀምሯል።
Editor at Hatricksport website