የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ከወልዋሎ አዲግራት ዩንቨርሲቲ እግር ኳስ ክለብ በቀረበለት የእግር ኳስ መጫወቻ ሜዳ ይታይልን ጥያቄ መሰረት በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የክለብ ፈቃድ ኃላፊ (Club Licensing Manager) በሆኑት አቶ ቴዎድሮስ ፍራንኮ የተመራ ሶስት አባላት ያሉት ቡድን ከጥር 22/2012ዓ.ም እሰከ ጥር 23/2012ዓ.ም የስታዲየም ምልከታ አካሄደ፡፡
ጉብኙቱን ያካሄደው ቡድንም በሪፖርቱ የአዲግራት ስታዲየም መጫወቻ ሜዳው ከተመልካች ጋር የሚለይበት አጥር ያለው እንደሆነ መጫወቻ ሜዳው ሙሉ በሙሉ የተፈጥሮ ሳር የለበሰ እንዲሁም ተቀያሪ ተጫዋቾች እና አራተኛ ዳኛ የሚቀመጡባቸው ቦታዎች እንደተዘጋጁ እና ሜዳው በግልጽ የሚታይ መስመር የተሰመረበት መሆኑን በሪፖርቱ አረጋግጧል፡፡
በእድሳት ላይ የሚገኘው የወልዋሎ አዲግራት ዩንቨርሲቲ እግር ኳስ ክለብ ስታዲየም ለሁለት ተጋጣሚ ቡድኖች የሚሆን የልብስ መቀየሪያ ክፍሎች ለእያንዳንዳቸው ቡድኖች 8 መታጠቢያ እና 8 መጻዳጃ ክፍሎች ያለው ሲሆን የሁለቱም ቡድኖች ልብስ መቀየሪያ ክፍሎች መቀመጫ ወንበሮች ያሏቸው ብሎም የህክምና ክፍል እና ለአካል ጉዳተኞች የሚሆኑ መጸዳጃ ክፍሎች መዘጋጀታቸውን የግምገማ ቡድኑ ተመልክቷል፡፡
- ማሰታውቂያ -
በስታዲየሙ የባለሜዳው ቡድን እና የእንግዳው ቡድን ደጋፊዎችን የሚለይ አጥር ተሰርቷል፤የሚዲያ እና የጋዜጣዊ መግለጫ መስጫ ክፍሎች በመሰራት ላይ መሆናቸውን ቡድኑ ተመልክቷል፡፡
የጨዋታ ዳኞች ማረፊያ ክፍል ከሻወር እና መጸዳጃ ክፍሎች ጋር የተሰራ ሲሆን ክፍሉም አራት ወንበር እና 4 መደርደሪያዎችን አካቷል፡፡
መስተካከል የሚገባቸው የሚከተሉት ጉዳዮች መሆናቸውን ቡድኑ በጻፈው ሪፖርት ላይ ገልጻል፡፡
የስታዲየም ጽዳት
ከጎል ጀርባ ያሉት ክፍት ቦታዎች እና ከመጫወቻ ሜዳው አጠገብ ያለው የፍሳሽ ማስወገጃ ተጫዋቾች እና ዳኞች ላይ ጉዳት ሊያደርስ ስለሚችል በአስፈላገው መሳሪያ ቢሸፈን አደጋ እንደሚቀንስ በሪፖርታቸው ገልጸዋል፡፡
የወልዋሎ አዲግራት ዩንቨርሲቲ እግር ኳስ ክለብ የሚጠቀምበትን የአዲግራት ስታዲየምን ለማደስ እንዲያመቸው ካሳለፍነው የውድድር ዘመን ጀምሮ በሜዳው ማድርግ የሚገባውን ጨዋታ በሙሉ በትግራይ አለማቀፍ ስታዲየም በመጠቀም ላይ እንደሚገኝ ይታወቃል፡፡
Via – EFF