በ22ኛ ሳምንት የሶስተኛ ቀን ውሎ የመጨረሻ ጨዋታ በበርካታ ደጋፊዎች ታጅቦ የተደረገው የወላይታ ድቻ እና የባህርዳር ከተማ ያለ ግብ አቻ ተጠናቋል ።
ወላይታ ድቻዎች በ21ኛው ሳምንት በፋሲል ከተማ በተረቱበት ጨዋታ ላይ ከነበረው የመጀመሪያ አሰላለፍ አንድ ለውጥ ብቻ በማድረግ ደጉ ደበበን በመልካሙ ቦጋለ ምትክ ሲያሰልፉ ባህርዳር ከተማዎች ደግሞ በሳምንቱ በጅማ አባጅፋር በተረቱበት ጨዋታ ከነበረው ምርጥ 11 አምሰት ለውጦችን በማድረግ አቡበከር ኑሪ ፤ ሳለአምላክ ተገኝ ፤ ብርሀኑ ጥጋቡ ፤ አደም አባስ እና ግርማ ዲሳሳን በፋሲል ገብረሚካኤል ፤ ሰለሞን ወዴሳ ፍቅረሚካኣል አለሙ ፤ ሄኖክ ኢሳይያስ እና አብዱልከሪም ኒኪማ ምትክ ጨዋታውን እንዲጀምሩ አድርገዋል ።
በጨዋታው የመጀመሪያ አጋማሽ ቀዳሚ ደቂቃዎች ላይ በሜዳቸው በመጫወት ላይ የነበሩት ባህርዳር ከተማዎች በተሸላ የማጥቃት እንቅስቃሴ ያደረጉበት ሲሆን በተጋጣሚያቸው የወላይታ ድቻ ቡድን ላይ ከፍተኛ ጫና በመፍጠር የግብ ዕድሎችን ለማግኘት ጥረቶችን ማድረግ ችለው ነበር ። የጦና ንቦቹ በጠንካራ የመከላከል ስራ ላይ ተጠምደው የቆዩ ሲሆን በቁጥር በርከት ብለው ከኳስ ጀርባ በመገኘች የጣና ሞገዶቹን የማጥቃት እንቅስቃሴ ለመግታት ችለዋል ።
- ማሰታውቂያ -
ለበርካታ ደቂቃዎች የግብ ሙከራን ያላስመከተን ይህ ጨዋታ በ26ኛው ደቂቃ ላይ ቃልኪዳን ዘላለም ከሳጥን ውጪ አክርሮ የመታውን እና ኢላማውን ሳይጠብቅ የቀረውን ኳስ አስመልክቶናል ። በባህርዳር ከተማ በኩል 33ኛው ደቂቃ ደቂቃ ላይ ፍፁም አለሙ ከርቀት ወደ ግብ ያደረገው የግብ ሙከራ በተመሳሳይ ወደ ውጪ ወጥቷል ።
ከሶስት ደቂቃዎች በኋላ ፈቱዲን ጀማል የፅዮን መርዕድ ከግቡ መውጣት ተመልክቶ ከርቀት ወደ ግብ የመታው ኳስ ለጣና ሞገዶቹ ሌላ የግብ ሙከራ ያደረጉበት ነበር ።
ቀስ በቀስ የባህርዳር ከተማን የኋላ ክፍል ማንኳኳት የጀመሩት የጦና ንቦቹ በመጀመሪያው አጋማሽ መጠናቀቂያ ደቂቃዎች በተቃረቡበት ጊዜ ጥሩ ጥሩ ዕድሎችን መፍጠር ችለቅ ሳይጠቀሙባቸው ቀርተዋል ።
38ኛው ደቂቃ ላይ እንድሪስ ሰይድ ከግራ መስመር አቅጣጫ የተገኘውን የቅጣት ምት በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ በአቡበከር ኑሪ ተመልሶበታል ። ከሰባት ደቂቃዎች በኋላ ቃልኪዳን ዘላለም በግራ መሰምር አቅጣጫ አምልጦ ወደ ሳጥን ይዞ የገባውን ኳስ ነፃ ለነበረው ያሬድ ዳዊት ለማቀበል ያደረገው ጥረት ያሬድ ኳሱን ሙሉ ለመሉ ማግኘት ባለመቻሉ ኳሱ ወደ ግብነት ሳይቀየር ቀርቷል ። የመጀመሪያው አጋማሽም ያለ ግብ ተጠናቋል።
በሁለተኛው አጋማሽ ባህርዳር ከተማዎች በተሻለ ጫና ማድረግ የቻሉ ሲሆን ከመጀመሪያው አጋማሽ በተሻለም ለግብ የቀረቡ የግብ ሙከራዎችን ማድረግ ችለው ነበር ። በአንፃሩ ወላይታ ድቻዎች አሁንም መከላከሉ ላይ ትኩረት በማድረግ በተወሰኑ አጋጣሚዎች ፈጣን የመልሶ ማጥቃቶችን ለመጠቀም ሞክረዋል ።
በ64ኛው ደቂቃ ላይ ኤርትራዊው አሊ ሱሌማን ከበረከት ጥጋቡ በረጅም የተሻገረለትን ኳስ የፅዮን መርዕድ መውጣት ተመልክቶ ወደ ግቡ መላክ ቢችልም ኳሱ ወደ ውጪ ወጥቶበታል ። በ76ኛው ደቂቃ ለይ ደግሞ የመሀል ተከላካዩ ፈቱዲን ጀማል የነጠቀውን ኳስ እየገፋ ሄዶ በጠንካራ ምት ወደ ግብ የላከው ኳስ የግቡን ቋሚ ለትሞ ተመልሷል ።
በመጨረሻዎቹ ደቂቃዎች ላይ የጣና ሞገዶቹ ከፍተኛ ጫና በመፍጠር በተለይም በተመስገን ደር አማካኝነት ያደረጓቸው የግብ ሙከራዎች በፅዮን መርዕድ ግብ ከመሆን ድነዋል ። በ81ኛው ደቂቃ ላይ ተመስገን ከሳጥንን ውጪ አክርሮ በመምታት የግብ ሙከራውን ያደረገ ሲሆን በተጨማሪ ደቂቃዎች ላየም ከማዕዘን በተነሳ ኳስ በመቀስ ምት ተቀልቦሶ ያደረገው ሙከራ በግብ ዘቡ ተይዞበታል ።
ውጤቱን ተከትሎ ወላይታ ድቻ ነጥቡን 35 በማድረስ ወደ 3ኛ ደረጃ ከፍ ሲል ባህርዳር ከተማ ደግሞ በ26 ነጥብ ወደ 10ኛ ከፍ ማለት ችሏል ።
በ23ኛ ሳምንት ጨዋታዎች በመጪው ግንቦት 4 ( ሀሙስ ) ረፋድ 4 ሰዓት ላይ ወላይታ ድቻ ቅዱስ ጊዮርጊስን ሲገጥም በተከታዩ ቀን ግንቦት 5 ( አርብ ) 10:00 ላይ ባህርዳር ከተማ ከፋሲል ከነማ ጋር ጨዋታውን ያደርጋል።