የኢትዮጵያ ፕሪሚየር የመጀመሪያ ዙር የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ ሲከናወኑ ሜዳው ላይ መቐለ 70 እ.ን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ 1-0 በማሸነፍ የመጀመሪያውን ዙር በድል ፈፅሟል።
በመጀመሪያው አጋማሽ ባለሜዳዎቹ ጫና ፈጥረው መጫወት የቻሉ ሲሆን እንግዳዎቹ ወደኋላ በማፈግፈግ በመልሶ ማጥቃት እና ረጃጅም ኳሶችን ሲጠቀሙ ተስተውለዋል።
ጨዋታው በተጀመረ 19ኛው ደቂቃ ላይ የድሬዳዋ ከተማው ሪቻሞንድ ኦዶንጎ አክርሮ የመታት ኳስ በግቡ አናት ላይ ወጥታለች። ባለሜዳዎቹ ተሽለው በታዩበት ጨዋታ በተደጋጋሚ የመቐለ 70 እንደርታን የግብ ክልል ሲፈትሹ ውለዋል። በዚህም 26ኛው ደቂቃ ላይ ሙኸዲን ሙሳ የሞከረው ኳስ ወደ ውጭ ወጥቷል። ከዚህች ሙከራ 6ደቂቃዎች በኋላ 32ኛውኛው ደቂቃ ላይ የድሬዳዋ ከተማው አማካይ ኤልያስ ማሞ ከርቀት የመታው ኳስ በግቡ አግዳሚ ለጥቂት ወጥታለች።
- ማሰታውቂያ -
ከዚህች ሙከራ በኋላም በተደጋጋሚ ሙከራ ለማድረግ ጥረት ያደረጉት ድሬዳዋ ከተማዎች ሲሆኑ እንግዳዎቹ መቐለ 70 እንደርታዎች ምንም አይነት ኢላማውን የጠበቀ ሙከራ ሳያደርጉ የመጀመሪያው አጋማሽ ተጠናቋል።
በሁለተኛው አጋማሽም የውጤት ጫና ውስጥ የሚገኙት ድሬዎች ጫና በመፍጠር ግብ ለማግኘት ሞክረዋል። መቐለ 70 እንደርታ ወደ ጨዋታው ለመግባት የፈጀባቸው 3ደቂቃዎች ብቻ ነበር። በ48ኛው ደቂቃ አማኑኤል ገብረሚካኤል ከርቀት አክርሮ የመታው ኳስ በአግዳሚው ለጥቂት ወጥቶበታል። ያን ያህል ሳቢ የሚባል እንቅስቃሴ ያልተስተዋለበት የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ 53ኛው ደቂቃ ሙኸዲን ሙሳ የመታው ኳስ ብረቱን ታኮ ወደ ውጪ ወጥቷል። ከዚህ በኋላም የረባ ሙከራ ሳይደረግበት ለረጅም ደቂቃዎች ቀጥሏል።
በመጨረሻም ጨዋታው ያለግብ በአቻ ውጤት ተጠናቀቀ ተብሎ ሲጠበቅ 90ኛው ደቂቃ ላይ ኤልያስ ማሞ ከማዕዘን ምት ያሻገረለትን ኳስ ዳኛቸው በቀለ ወደ ግብነት ቀይሮት ባለሜዳዎቹን ጣፋጭ ድል ማጎናጸፍ ችላለች። ጨዋታውም በድሬዳዋ ከተማ 1-0 አሸናፊነት ተጠናቋል።