የኢትዮጲያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ዲሲፕሊን ኮሚቴ ፋሲል ከነማና ቅዱስ ጊዮርጊስ ላይ ያስተላለፈውን የቅጣት ውሳኔ በመቃወም ፋሲል ከነማ ያቀረበው ይግባኝ ውድቅ ሆኗል፡፡
ዲሲፕሊን ኮሚቴ የፋሲል ከነማ ደጋፊዎች ዳኞቹ ላይ በመታፋት በመሳደብ ለድብደባ ሙከራ በማድረግ እንዲሁም ዳኞቹ ከሜዳ እንዳይወጡ በማድረግ ጥፋተኛ ሆነዋል፡፡ ዳኞቹም በፓትሮል ታጅበው የወጡት ከ20 ደቂቃ እገታ በኋላ መሆኑ በሪፖርቱ ተገልጿል በሚል አንድ ጨዋታ በገለልተኛ ሜዳ እንዲጫወቱና አወዳዳሪው አካል ሜዳውን እንዲመርጥ የ30 ሺህ ብር እንዲከፍሉም ወስኗል፡፡
ይህንን የገንዘብ ቅጣት በ7 ቀን ውስጥ እንዲከፍሉ ካልከፈሉ የቅጣቱ 2% በየቀኑ እንደሚጨምር በማስጠንቀቅ ይህ የማይሆን ከሆነ ከፌዴሬሽኑ ጽ/ቤት ምንም አይነት ግልጋሎት እንዳያገኙ መወሰኑ የሚታወስ ሲሆን ክለቡም ይግባኝ ጠይቆ እንደነበር የሚታወስ ነው፡፡
የፌዴሬሽኑ የይግባኝ ሰሚ ኮሚቴ ይግባኙን ከመረመረ በኋላ የዲሲፕሊን ኮሚቴ ውሳኔ ምንም አይነት የህግ ክፍተት የሌለበት ተገቢ ውሳኔ ነው ሲል ውሳኔውን በማፅናት ፋሲል ከነማ ያስያዘው የይግባኝ መጠየቂያ 1500 ብር ለፌዴሬሽኑ ገቢ እንዲሆን ወስኗል፡፡
በዚህ መሠረት በ16ኛ ሳምንት መርሃግብር ከአዳማ ከተማ ጋር የሚካሄደውን ጨዋታ ከሜዳ ውጪ ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡