በያዝነው የውድድር ዘመን በኢትዮጵያ ቡና ጎልተው ከታዩ ተጫዋቾች አንዱ የሆነው ፈቱዲን ጀማል ከክለቡ ጋር መለያየቱ ዕውን ሆናል
ፈቱዲን ጀማል ከደቂቃዎች በፊት ለቀድሞ ክለቡ ሲዳማ ቡና በመፈረም ከኢትዮጵያ ቡና ጋር በይፋ መለያየቱን አረጋግጧል።
ኢትዮጵያ ቡናና ፈቱዲን ጀማል ከአንድ ወር ቀሪ ደሞዝና ከጥቅማ ጥቅም ጋር በተያያዘ ሲያደርጉት የነበረው ድርድር ፍሬ ሊያፈራ ባለመቻሉ በመጨረሻም ለመለያየትና የተጫዋቹ ማረፊያ ሲዳማ ቡና ሊሆን ችሏል።
የኢትዮጵያ ቡና አሠልጣኝ ካሳዬ አራጌ ወደ ኢትዮጵያ ከመጣ በሃላ ተጫዋቹ ክለቡን እንዳይለቅ በተንቀሳቃሽ ስልኩ ላይ ደውሎ ቢያናግረውም ሊስማሙ ባለመቻላቸው ከቡና ጋር የነበረው ቆይታ በአንድ ዓመት ተጠናቋል።
ፈቱዲን ለሲዳማ ቡና ለሁለት ዓመት የፈረመ ሲሆን የተሻለ ደሞዝና ከፍተኛ ጥቅም እንደቀረበለት ነው የክለቡ ምንጮች በተለይ ለሀትሪክ የገለፁት።
ፈቱዲን ጀማል ከኢት.ቡና ሲለቅ አራተኛው ተጫዋች ሲሆን ከእሱ በፊት አማኑኤል ዮሐንስና አህመድ ሽሪላ ወደ ባህር ዳር፣ግብ ጠባቂው በረከት ወደ መቖለ 70 አንደርታ መዛወራቸው ይታወሳል።