ከአቶ ጁነዲን ይልቅ ሱዳናዊው ማግዳ ሸምስ የተሻለ ዕድል እንዳላቸው እየተነገረ ነው
የሀትሪክ ጋዜጣ ማኔጂንግ ኤዲተር –በይስሃቅ በላይ
የዳዊትና የጎልያድ ፍልሚያ
የተባለ ስያሜ ከተሰጠው የኢሳ
ሃያቱና የማዳጋስካሩ አህመድ
አህመድ የፕሬዘዳንትነት ፍጥጫ
ባልተናነሰ ለካፍ ስራ አስፈፃሚ
አባልነት የሚደረገው ሩጫ
ከወዲሁ የብዙዎችን ትኩረት
እየሳበ ይገኛል፡፡
በዚህ በኩል
በተለይ 13 አባል አገራትን የያዘው
የምስራቅና መካከለኛው አፍሪካ
አገሮች (ሴካፋን) በመወከል
በካፍ ውስጥ ወንበር ለማግኘት
የሚደረገው ትንቅንቅ ብዙዎች
ጆሮአቸውን እንዲሰጡ ብቻ
ሳይሆን የምርጫው ቀን ደርሶ
ማን ምርጫውን በአሸናፊነት
ያጠናቅቃል? የሚለውን በጉጉት
እንዲጠብቁት አድርጓል፡፡
ቀደም ሲል 13 አባል አገራት
ያሉትና ሴካፋን በመወከል ለስራ
አስፈፃሚነት ለመወዳደር የአራት
አገራት ፌዴሬሽኖች ተወካዮች
ማለትም የኢትዮጵያ እግር ኳስ
ፌዴሬሽን ፕሬዘዳንት አቶ ጁነዲን
ባሻህ፣ የሱዳን እግር ኳስ ፌዴሬሽን
ዋና ፀሃፊ ሸምስ ማግዳ፣የጅቡቲ
እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዘዳንት
እና የኡጋንዳ አቻቸው ራሳቸውን
የምርጫ እጩ አድርገው
ዘመቻቸውን በይፋ ቢጀምሩትም
ምርጫው በጣት የሚቆጠሩ
ቀናት ቢቀሩቱም በመጨረሻው
ሰአት ፉክክሩ በአቶ ጁነዲንና
በሱዳናዊው ሸምስ ማግዳ መካከል
ሆኗል፡፡
የካፍ ፕሬዘዳንታዊና የስራ
አስፈፃሚ ኮሚቴ አባላት የሁለት
ቀናት እድሜ ብቻ እየቀረው
ከሱዳን እግር ኳስ ፌዴሬሽን
ዋና ፀሃፊ ጋር ለካፍ ስራ
አስፈፃሚነት የጠነከረ ብርቱ
ፉክክር በመጨረሻው ሰአት ላይ
የገጠማቸው አቶ ጁነዲን ባሻህ
ቀደም ሲል ኢትዮጵያ የካፍ
መስራች፣ የዞኑም ሃያል የእግር
ኳስ አገር እንዲሁም የአፍሪካ
ዋና ከተማ ከመሆንዋ አንፃር
እድሉ ለኢትዮጵያ መሰጠት
አለበት በሚል አቋም በመያዙ
አቶ ጁነዲን ባሻህ ከሌሎች
ተፎካካሪዎች በተሻለ ለቦታው
ቀዳሚው ሰው ተደርገው
እንዲገመቱ ቢያደርጋቸውም አቶ
ጁነዲን ባሻህ ባለፈው ሐሙስ ወደ
ዚምባብዌ ተጉዘው የካፍ ፕሬዘዳንት
ኢሳ ሃያቱ ዋነኛ ተቀናቃኞችና
ወንበራቸውን ለመገርሰስ ጠንክረው
እየሰሩ ከሚገኙት የ13 አገራት
ፌዴሬሽን ፕሬዘዳንቶች፣ የፊፋ
ፕሬዘዳንት ኢንፋንቲኖ፣ የፊፋ
ዋና ፀሃፊ ፋቲማ ሳምባ በተገኙበት
በሬይንቦው ታወርስ በተደረገው
ስብሰባና የዚምባባዌ እግር ኳስ
ፌዴሬሽን ፕሬዘዳንት የልደት
በዓላቸው ላይ መገኘታቸው
በምርጫው አስቀደሙው እጅ
ለሰጡት ሱዳናዊው ሽምስ ማግዳ
ያልታሰበ ሲሳይ ይዞላቸው ብቅ
ብሏል፡፡
አቶ ጁነዲን ባሻህ ኢሳ ሃያቱን
ለ29 ዓመታት ከተቀመጡበት
ወንበር ፈንቅለው ለመጣልና
በምትካቸው የማዳጋስካሩን የቀድሞ
ሚኒስትርና የፌደሬሽኑ ፕሬዘዳንት
የሆኑትን አህመድ አህመድን ወደ
ስልጣን ለማምጣት እየተረባረቡ
ከሚገኙትና ይሄንን በዋናነት
ከሚያስተባብሩት የናይጄሪያ
እንዲሁም የዚምባብዌ እግር ኳስ
ፌዴሬሽን ፕሬዘዳንት የልደት በዓል
ላይ መገኘታቸው በኢሳ ሃያቱ ወገን
ያሉትን ደጋፊዎች ከማስቆጣቱም
በላይ አቶ ጁነዲን ወደ ዚምባብዌ
ሄደው የኢሳ ሃያቱን የስልጣን ዘመን
እንዲያበቃ እንቅልፍ ከሚያጡ
ወገኖች ጋር መሰብሰባቸውና
የፕሬዘዳንቱን የልደት በዓል ኬክ
ቆርሰው ማክበራቸው በተዘዋዋሪ
ለእጩው ፕሬዘዳንት የምርጫ
ተፎካካሪ አህመድ አህመድ ድጋፍ
ለመስጠት የሚል ድምዳሜ ላይ
እንዲደርሱ በማድረጉ በኢሳ ሃያቱ
ወገን ያሉ መራጮች ድምፃቸውን
ከአቶ ጁነዲን ባሻህ ይልቅ የኢሳ
ሃያቱ ደጋፊ ለሆኑት ለሱዳናዊው
ሸምስ ማግዳ እንዲሰጡ ውስጥ
ለውስጥ የተለያዩ የቅስቀሳ ስራዎች
መሰራት በመጀመራቸው ዕድል
ከአቶ ጁነዲን ባሻህ እጅ አፈትልካ
መውጣትዋን ነው ውስጣዊ
ምንጮች እየጠቆሙ ያሉት፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ
ፌደሬሽንን ውክልና በማግኘት ለካፍ
የስራ አስፈፃሚነት በመወዳደር ላይ
የሚገኙት አቶ ጁነዲን ባሻህ ከደቡብ
አፍሪካ ወደ ዚምባብዌ የተጓዝኩትና
በልደት በዓሉ ላይ የተገኘሁት
የአገሮችን ድምፅ ለማግኘትና መራጮችን
ለማግባባት በማሰብ ብቻ ነው በማለት
የሚቀርብባቸውን ወቀሳ ለማስተባበል
ሙከራ ቢያደርጉም ማስተባበያው በኢሳ
ሃያቱ ወገን ያሉትን መራጮች ማሳመን
ባለመቻሉ ድምፆች ሁሉ እግር አውጥተው
ወደ ሱዳናዊው ተወዳዳሪ በማዘንበላቸው
አቶ ጁነዲን በመጨረሻው ሰአት በፈፀሙት
ስህተት አገራችን በካፍ ስራ አስፈፃሚነት
ልታገኘው የነበረው እድል መጨናገፉንና
በእሳቸው ምትክ ሱዳናዊው ሸምስ ማግዳ
ቦታውን ሊያገኙ እንደሚችሉ ነው ለወሬው
በጣም ቅርብ ነን የሚሉ ሰዎች ከምርጫው
ሁለት ቀናት በፊት እየገለፁ ያሉት። አቶ
ጁነዲን ባሻህ በቀሪዎቹ ቀናት ይሄንን
አመለካከት በመስበር እድሉ ከኢትዮጵያ
በማይወጣበት መንገድ ላይ ጠንክረው
መስራት እንደሚገባቸውም ምክራቸውን
ለግሰዋል፡፡