የ2010 የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የውድድር ዘመን ፍፃሜውን ሲያገኝ አዲስ አዳጊው ጅማ አባጅፋር የውድድሩ አሸናፊ መሆን ችሏል። አ/አ ስታዲየም ላይ ቅ/ጊዮርጊስ ሀዋሳ ከተማን አስተናግዶ 2-0 በሆነ ውጤት ቢያሸንፍም በጅማ አባ ጅፋር በግብ ክፍያ ተበልጠው የሊጉን ዋንጫ ማንሳት ሳይችሉ ቀርተዋል፡፡
የክረምቱን መግባት ተከትሎ እንደ ሰሞኑ ሁሉ ጨቅይቶ የነበረው የስታዲየሙ መጫወቻ ሜዳ በዝናብ ምክንያት ውሃ ቋጥሮ ለተጨዋቾች አስቸጋሪ ሁኔታን ሲፈጥር ተስተውሏል፡፡ የሜዳውም አስቸጋሪ መሆን ሁለቱም ቡድኖች ያላቸውን ነገር ማሳየት ሲሳናቸው ተስተውሏል።
- ማሰታውቂያ -
በመጀመሪያው 45 የጨዋታ ክፍለጊዜ እንግዳዎቹ ሀዋሳ ከተማዎች በመከላከል አልፎ አልፎ በመልሶ ማጥቃት ሲጫወቱ የነበረ ሲሆን ጊዮርጊሶች በአንፃሩ ጫና ፈጥሮ በመጫወት ቶሎ ግብ ለሚስቆጠር ሲጥሩ ታይተዋል፡፡ አብዛኛውን የመጀመሪያ አጋማሽ ሁለቱም ቡድኖች መሀል ሜዳ ላይ ያደላ እንቅስቃሴ ይታይ ነበር፡፡
በሀዋሳ ከተማ በኩል 22ኛው ደቂቃ ላይ ፍቅረየሱስ ተወልደብርሃን ከፍፁም ቅጣት ምት ሳጥን አቅራቢያ ያገኘውን ክፍተት ተጠቅሞ መሬት ለመሬት የመታው ኳስ ለጥቂት ወጥቶበታል፡፡
ቅ/ጊዮርጊስ በአንፃሩ በፍጥነት ግቦችን ለማስቆጠር ያለመ እንቅስቃሴን በመጀመሪያው አጋማሽ አድርገዋል፡፡ 30ኛው ደቂቃ ላይ የቅ/ጊዮርጊሱ በኃይሉ አሰፋ ላይ የተሰራውን ጥፋት ተከትሎ ባለሜዳዎቹ የፍፁም ቅጣት ምት አግኝተዋል የነበረ ቢሆንም ሳላዲን ባርጌቾ መቶት ግብ ጠባቂው ተክለማሪያም ሻንቆ መልሶበታል፡፡ ከ6ደቂቃዎች በኋላ 36ኛው ደቂቃ ላይ ከማዕዘን የተሻረገውን ኳስ ሳላዲን ወደ ግብነት ቀይሮት ጊዮርጊሶች መምራት ጀምረው ወደ መልበሻ ቤት አምርተዋል።
ከእረፍት መልስም በተደጋጋሚ ወደ ሀዋሳ ከተማ የግብ መድረስ የቻሉት ፈረሰኞቹ ሁለተኛውን ግብ ለማግኘት 15ደቂቃዎች ብቻ ነበር የፈጀባቸው። 60ኛው ደቂቃ ላይ ከቅጣት ምት የተሻገረውን ኳስ ነፃ አቋቋም ላይ የነበረው ሙሉአለም መስፍን(ዴኮ) በግንባሩ ገጭቶ በማስቆጠር መሪነቱን መሪነቱን ወደ 2-0 ከፍ ማድረግ ችሏል። ከዚህ ግብ መቆጠር በኋላ ይሄ ነው የሚባል የረባ እንቅስቃሴ ሳይታይበት ጨዋታው በቅ/ጊዮርጊስ 2-0 አሸናፊነት ተጠናቋል።
ውጤቱንም ተከትሎ ቅ/ጊዮርጊስ ከጅማ አባ ጅፋር ጋር በእኩል 55 ነጥብ ሊጉን ቢያገባድም በግብ ክፍያ ተብልጦ በሁለተኛ ደረጃነት አጠናቋል፡፡