ለአሰልጣኝ ስዩም አባተ በተዘጋጀው የመታሰቢያ ውድድር አራቱ ለግማሽ ፍፃሜ ያለፉት ቡድኖች ታውቀዋል፤ ዐርብ ጨዋታው ይቀጥላል
የኢትዮጵያ ስፖርት ታሪክ ውስጥ በተጨዋችነትም በአሰልጣኝነትም በሙያቸው ትልቅ ግልጋሎትን ሰጥተው ላለፉት እና በቅርቡ በሞት ለተለዩት አሰልጣኝ ስዩም አባተ የተዘጋጀው የመታሰቢያ ውድድር በ6 የብሔራዊ ሊግ ክለቦች መካከል በቄራ አልማዝዬ ሜዳ ሲካሄድ ቆይቶ ዛሬ የምድብ ጨዋታዎቹ ሊጠናቀቁ ችለዋል፤ ዛሬ በተካሄደው ጨዋታም ከምድብ አንድ ቄራ አንበሳ ቂርቆስ ክፍለ ከተማን 3ለ0 በመርታት ወደ ግማሽ ፍፃሜው ሁለተኛ ሆኖ ሲያልፍ ንፋስ ስልክ ላፍቶ አሰቀድሞ ባደረጋቸው ጨዋታዎች ቄራ አንበሳን በማሸነፍና ከቂርቆስ ክፍለ ከተማ ጋር አቻ በመለያየት ከምድቡ አንደኛ ሆኖ አልፏል፡፡
በዛሬው ሌላኛው የምድብ ሁለት ጨዋታ የልደታ ክፍለ ከተማ እግር ኳስ ቡድን የአዲስ አበባ ፖሊስ እግር ኳስ ክለብን በፍርፌ በማሸነፍ ከምድቡ አንደኛ ሆኖ ለግማሽ ፍፃሜ ያለፈ ሲሆን፤ ሌላው የእዚህ ምድብ ተሳታፊ የነበረው ናኖ ሁርቦ ምንም እንኳን በሁለተኛው ጨዋታው በልደታ ቢሸነፍም ቀደም ሲል ባደረገው ጨዋታ አዲስ አበባ ፖሊስን 3-1 በመርታቱ ከምድቡ ሁለተኛ ሆኖ አልፏል፡፡
የአሰልጣኝ ስዩም አባተ የመታሰቢያ ዋንጫ የግማሽ ፍፃሜ ጨዋታ ዐርብም የሚቀጥል ሲሆን በዕለቱም የሚጫወቱት ቡድኖች ንፋስ ስልክ ላፍቶ ከናኖ ሁርቦ እንደዚሁም ደግሞ ልደታ ክፍለ ከተማ ከቄራ አንበሳ ጋር መሆናቸውም ታውቋል፡፡
የአሰልጣኝ ስዩም አባተ የመታሰቢያ ውድድር እሁድ ፍፃሜውን ሲያደርግም የግማሽ ፍፃሜ አሸናፊዎቹ ለዋንጫ የሚጫወቱ ሲሆን በሌላው የዋንጫ ጨዋታ በመክፈቻው ቀን ግጥሚያ አቻ የተለያዩት የቀድሞ የቡና ተጨዋቾች እና የቄራ አንበሳ የጤና ቡድን የሚጫወቱ ይሆናል፡፡