በትግራይ ስታድየም የተካሄደው የመቐለ 70 እንደርታና ኢትዮጵያ ቡና ጨዋታ ሁለቱም ቡድኖች በመጀመርያ አጋማሽ ባስቆጠርዋቸው ግቦች ታጅቦ በአቻ ውጤት ተጠናቋል።መቐለ 70 እንደርታ በባህርዳር ከተማ ከተሸነፈው ስብስብ ሥስት ቅያሬዎችን ላውረንስ ኤድዋርድ በአሌክስ ተሰማ፣ሳሙኤል ሳሊሶ በአሸናፊ ሃፍቱ፣ዳንኤል ደምሱ በቢያድግልኝ ኤልያስ ሲቀይሩ ኢትዮጵያ ቡናዎች በበኩላቸው ጅማን ከገጠመው ስብስብ ታፈሰ ሰለሞንን በፍቅረየሱስ ተክለብርሃን ቀይረው ወደ ሜዳ ገብተዋል።
የኢትዮጵያ ቡና የኳስ ቁጥጥር ብልጫ በታየበት የመጀመርያ አጋማሽ የካሳዬ አራጌ ቡድን ከኃላ ኳስን በመመስረት ተጋጣምያቸውን በአጫጭር ቅብብሎች በማስከፈት እድሎችን መፍጠር ችለዋል።በተለይ ግራ መስመር ላይ የተሰለፈው አቡበከር ነስሩ ከእንዳሌ ደባልቄ ጋር የነበራቸው ጥምረት ለመቐለ ተከላካይ ክፍል ፈተና ሆኖ ታይቷል።የዚህ ማሳያ ሚሆነው አቡበከር ከግራ መስመር ሰብሮ በመግባት ከእንዳለ አንድ ሁለት ተጫውቶ የመታው ኳስ ኦቮኖ በቀላሉ ሊመልስለት ችሏል።በመጀመርያው አጋማሽ ጥሩ ያልነበሩት መቐለዎች በግል በጨዋታው ላይ ጥሩ በነበሩት አማኑኤል ገብረሚካኤል ጥምረት የተገኘችውን ኳስ አሸናፊ ሃፍቱ በአግባቡ ተጠቅሞ ሻምፒዮኖቹን መሪ ማድረግ ችሏል።ሆኖም መቐለ 70 እንደርታዎች መሪነታቸውን ከእምስት ደቂቃ በላይ ማቆየት ተስንዋቸው በ14ኛው ደቂቃ በእንዳለ ደባልቄ ጥሩ አጨራረስ መሪነታቸው ተነጥቀዋል።ከግቡ በኃላ ጥሩ መነሳሳት ያሳዩት ኢትዮጵያ ቡናዎች የጨዋታውን ፍጥነት በመቆጣጠር በፍቅረየሱስ ተክለብርሃን እንዲሁም በእንዳለ ደባልቄ ከርቀት ሙከራዎችን ቢያደርጉም ዒላማቸውን የጠበቁ አልነበሩም።መቐለዎች በበኩላቸው መስመር ላይ ትኩረት አድርገው እድሎችን ለመፍጠር ቢምክሩም የጠራ የግብ እድል መፍጠር ሳይችሉ ቀርተዋል።
- ማሰታውቂያ -
ሁለተኛው አጋማሽ የቡና ተጨዋቾች ተደጋጋሚ ሜዳ ላይ መውደቅ የታየበት መቐለዎች ከመጀመርያው አጋማሽ ተሽለው ጫና ፈጥረው የተጫወቱበት ነበር።በተለይ መቐለዎች መጀመርያ ላይ የነበራቸውን ክፍተት በመጠኑም በመቅረፍ ኢላማቸውን የጠበቁ ሙከራዎችን በያሬድ ከበደ ና ቢያግልኝ ኤልያስ ቢያደርጉም ጨዋታው ላይ ጥሩ በነበረው ተክለማርያም ሻንቆ ድንቅ ብቃት ሊመለሱ ችለዋል።ኢትዮጵያ ቡናም በሁለተኛው አጋማሽ የመጀመርያ ደቂቃዎች ላይ በእንዳለ ደባልቄ ና አቡበከር ነስሩ አማካኝነት ጥሩ እድሎችን ቢያገኙም ሳይጠቀሙበት ቀርተዋል።በዚህም መሰረት ከ45ሺህ በላይ ደጋፊዎች የታደሙበት ጨዋታ በአቻ ሊጠናቀቅ ችሏል።
ውጤቱን ተከትሎ መቐለ 70 እንደርታ ነጥባቸውን ወደ 4 ከፍ ሲያደርጉ እንግዳዎቹ ኢትዮጵያ ቡናም የዓመቱ ከሜዳቸው ውጪ የመጀመርያ ነጥብ ማግኘት ችለዋል።