የኢትዮጵያ ፌዴሬሽን በሚያዘጋጃቸው በሁሉም ውድድሮች የዓመቱን ምርጥ ተጫዋች፣ ምርጥ ግብ አግቢ፣ ምርጥ ግብ ጠባቂና ምርጥ አሰልጣኝ ትናንት ምሽት በካፒታል ሆቴል ባዘጋጀው የእራት ፕሮግራም ላይ ዕውቅና ሰጠ፡፡
በተጨማሪ ፌዴሬሽኑ ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ዕድገት ልዩ አስተዋጽ አድርገዋል ላላቸው የቀድሞው የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን አለቃ ክቡር ይድነቃቸው ተሰማ የልዩ የህይወት ዘመን ሽልማት ሰጥቷል፡፡
በሽልማቱ ላይ ከይድነቃቸው በተጨማሪ ኢንተርናሽናል የመሃል ዳኞች ባምላክ ተሰማ፣ ሊዲያ አሰፋና ኢንተርናሽናል ረዳት ዳኛ ተመስገን ሳሙኤል እንዲሁም የኢትዮጵያ ቡናውና የብሔራዊ ቡድኑ ፊዚዮቴራፒስት ይስሃቅ ሽፈራው ልዩ እውቅና ተሰጥቷቸዋል፡፡
የፋሲል ከነማና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የመሃል ሜዳ ተጫዋች ሱራፌል ዳኛቸው ዓመቱን ሙሉ ባሳየው ወጥ ብቃት የመቀሌውን አጥቂ አማኑኤል ገብረሚካኤልንና የሲዳማ ቡናውን አጥቂ ሃብታሙ ገዛኸኝን በልጦ የዓመቱ ምርጥ ተጫዋችን ሽልማት ወስዷል፡፡
በሊጉ በርካታ ጎል በማግባት አማኑኤል የዓመቱ ምርጥ ግብ አግቢ ተብሎ ሲሸለም የክለብ አጋሩ የኢኳቶሪያል ጊኒው ግብ ጠባቂ ፌሊፕ ኦቮኖ የዓመቱ ምርጥ ግብ ጠባቂ ሽልማትን ወስዷል፡፡
በሴቶች ዘርፍ የአዳማ ከተማ ተጫዋቾች ሁሉንም ሽልማት ጠቅልለው ሲወስዱ የቡድኑ አጥቂ ሴናፍ ዋቁማ የዓመቱ ምርጥ ግብ አግቢና ምርጥ ተጫዋች ሽልማትን ወስዳለች፡፡ የቡድን አጋሯ እምወድሽ ይርጋ ደግሞ የዓመቱ ምርጥ ግብ ጠባቂ ተብላ ተሸልማለች፡፡
ሱራፌል ዳኛቸው የዓመቱ ምርጥ ተጫዋች ሽልማትን አገኘ
Editor at Hatricksport