በ2ኛው ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ትግራይ ስታድየም ላይ ወላይታ ድቻን ያስተናገዱት ወልዋሎዎች በካርሎስ ዳምጠው ና ሰመረ ሀፍታይ ሁለት ግቦች ታግዘው ሁለተኛ ተከታታይ ድላቸውን አመዝግበዋል።
አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ በመጀመርያው ሳምንት ሰበታ ላይ ድል ካስመዘገበው ምርጥ 11 ጁልያስ ናንጂቡ ና ኢታሙና ኩሜይኒን በሰመረ ሀፍታይ ና ራምኬል ሎክ ቀይረው ወደ ሜዳ ገብተዋል።ወላይታ ድቻዎች በተመሳሳይ ሲዳማ ቡናን ካሸነፈው ስብስብ ሁለት ቅያሬዎችን አድርገዋል።ባዬ ገዛሀኝን በዳንኤል ዳዊት፣እዮብ አለማየሁን በፀጋዬ አበራ በመተካት ጨዋታውን ጀምረዋል።በመጀመርያው አጋማሽ ባለ ሜዳዎቹ ወልዋሎዎች ቀጥተኛ በሆኑ ኳሶች ፊት ላይ ለተሰለፋት ካርሎስ ዳምጠው እና ሰመረ ሀፍታይ ኳስ በተደጋጋሚ እንዲደርስ በማድረግ ዕድሎችን ለመፍጠር ሲሞክሩ ታይቷል፤የዚህ እንቅስቃሴ ውጤትም ጨዋታው በተጀመረ በ3ኛው ደቂቃ በካርሎስ ዳምጠው አስደናቂ ግብ ሊታጀብ ችልዋል።ካርሎስ በወላይታ ድቻ ፍፁም ቅጣት ሳጥን ውስጥ በቀኝ በኩል ያገኛትን ኳስ በግራ እግሩ አክርሮ በመምታት ክለቡን ወልዋሎ መሪ እንዲሆን በማድረግ በተከታታይ ጨዋታ ግብ አስቆጥርዋል።በአጫጭር ቅብብል ኳስን ከኃላ በመመስረት እድሎችን ለመፍጠር የሞከሩት ወላይታዎች የመጅመርያ 30 ደቂቃዎች ላይ ተቸግረው ቢታዩም፣በመጀመርያ አጋማሽ የመጨረሻ 15 ደቂቃዎች ላይ ጫና ፈጥረው ተጫውተዋል።በተለይ በ1ኛው ደቂቃ አይናለም ሀይሉ ኳስን ወደ ኃላ ለመመለስ በሚሞክርበት ጊዜ በፈጠረው ስህተት ዳንኤል ዳዊት ያገኛት ግልፅ የማግባት እድል በአብዱላዚዝ ኬይታ ብቃት ሊከሽፍ ችሏል በተጨማሪ በግምት ከ20 ሜትር ተስፋዬ አለባቸው የመታው ጠንካራ ኳስ ከግቡ አናት ለትንሽ ወጥቷል።አቻ ሚያደርጋቸውን ግብ ለማግኘት ቀኝ መስመር ላይ ትኩረት አድርገው የተንቀሳቀሱት ወላይታ ዲቻዎች በ37ኛው ደቂቃ ጥረታቸው ተሳክቶ በፀጋዬ ብርሀነ የግምባር ኳስ አማካኝነት አቻ ሚያደርጋቸው ግብ አስቆጥረዋል።የቀኝ መስመር ተመላላሹ ፀጋዬ አበራ ያሻማው ኳስ ፀጋዬ ብርሀነ በአስደናቂ አጨራረስ አብዱላዚዝ ኬይታን ምንም ዕድል ሳይሰጥ ሊያስቆጥረው ችሏል።በዚህም መሰረት የመጀመርያው አጋማሽ በአቻ ውጤት ተጠናቋል።
- ማሰታውቂያ -
በሁለተኛው አጋማሽ የመጀመርያ 15 ደቂቃዎች ላይ የተሻለ የተንቀሳቀሱት ወልዋሎዎች በካርሎስ ዳምጠው እና ሰመረ ሀፍታይ አማካኝነት ያደረጉዋቸው ሙከራዎች በግብ ጠባቂው መክበብ ደገፋ ተመልሰዋል።ሆኖም በ59ኛው ደቂቃ ከቀኝ መስመር የተሻማውን ኳስ በጥሩ ወቅታዊ አቋም ሚገኘው ሰመረ ሀፍታይ በሚገባ ተቆጣጥሮ በመምታት ወልዋሎ ከጨዋታው ሙሉ ሥስት ነጥብ እንዲያገኝ አስችሎታል።ዲቻዎች በድጋሜ ወደ ጨዋታው ለመመለስ ያደረጉት ሙከራ በወልዋሎ ጠጣር መከላካል ሳይሳካላቸው ቀርቷል።
ወልዋሎዎችም የ2ለ1 መሪነታቸውን በማስጠበቅ በሊጉ አናት ላይ ሊቀመጡ ችለዋል።