በ8ኛ ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ መርሐ ግብር ዛሬ አንድ ጨዋታ የተከናወነ ሲሆን በጨዋታውም ሰበታ ከተማ ጅማ አባጅፋርን 3-1 በሆነ ውጤት አሸንፏል። ከጨዋታ በኋላም የሁለቱ ቡድን አሰልጣኞች አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
የሰበታ ከተማው ውበቱ አባተ “ለእኛ ጨዋታው መጥፎ አልነበረም። ከጨዋታው በፊት ጅማዎች በጣም ወደ ኋላ አፈግፍገው ይጫወታሉ ብለን ነበር አስበን የመጣነው። ያገኘነውም ይሄንኑ ነው።” ብለዋል። አክለውም “ግቡን ካስቆጠርን በኋላ ወጥተው ለመጫወት ሞክረዋል።” በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል። ስለ ቡድኑ የራስ መተማመን የተጠየቁት አሰልጣኙ “ማንኛውም ዓይነት ተጫዋች ቢኖርህ ሥነ ልቦና ከሌለህ ዋጋ የለውም። በእንቅስቃሴ ብቻ ሳይሆን በሥነ ልቦናውን ረገድ ከእለት ወደ እለት መሻሻሎች አሉ።” ሲሉ መልሰዋል። በመጨረሻም አሰልጣኙ “በአጠቃላይ በሽሬ ከተሸነፍንበት ጨዋታ ውጪ ምንም መጥፎ ውጤት ከሜዳችን ውጪ የለም።” ሲሉ መግለጫቸውን አጠናቀዋል።
የጅማ አባጅፋሩ ጳውሎስ ጌታቸው በበኩላቸው ቡድናቸው ከ72 ሰዓታት ባነሰ ጊዜ እንዲጫወቱ መደረጋቸው ስህተት እንደነበር እና በስራ አስኪያጃቸው በኩል ቅሬታ ቢያቀርቡም ሜዳው ነገ ተይዟል መባላቸውን አምርረው ተናግረው ይህንን ግን እንደ ሰበብ መጠቀም እንደማይፈልጉ እና እሳቸውም ሆኑ ተጫዋቾቻቸው ውጤቱን በፀጋ እንደሚቀበሉ ገልፀው በቀጣይ ግን ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚፈለገውን ሥራ እንሰራለን። በማለት አስተያየታቸውን ቋጭተዋል።