የኢትዮጵያ ስፖርት ጋዜጠኞች ማኅበር ጠቅላላ ጉባዔውን በአዲስ አበባ ኢንተር ኮንትኔታል ሆቴል አካሂዷል።
የኢትዮጵያ ስፖርት ጋዜጠኞች ማኅበር በዓመቱ ሊሰራቸው ካቀዳቸው አብዛኛዎቹን አለማከናወኑን ገለጸ።
የማኅበሩ ፕሬዚዳንት ጋዜጠኛ ዮናስ ተሾመ እንደገለጸው፤ ማኅበሩ በዓመቱ ለመሥራት ከያዛቸው ዕቅዶች አብዛኛዎቹን አላከናወነም።
በእቅዶቹ መሰረት ተግባራዊ ያለመሆን በዋነኛ ምክንያትነት የተነሳው አንዳንድ ሥራ አስፈጻሚዎች ከአገር መውጣታቸውና ሌሎችም የሙሉ ጊዜ ሠራተኞች ባለመሆናችው የተፈጠረ ክፍተት ነው።
ማኅበሩ በዕቅድ ይዞ ካልተገበራቸው ሥራዎች መካከል የራሱን የገቢ ምንጭ የማስፋፋትና የማሳደግ፣ ለስፖርት ጋዜጠኞች ሥልጠናዎችን የማመቻቸትና የአባላቱን ቁጥር የማሳደግ የሚሉት ተጠቃሽ ናቸው።
በጠቅላላ ጉባዔው እንደ ችግር ከተነሱት መካከል የማኅበሩ አባላት የአባልነት ክፍያቸውን በአግባቡ አለመፈጸም ይገኝበታል።
- ማሰታውቂያ -
የውጭ ጉዞን በተመለከተ ጋዜጠኞች በተደጋጋሚ ቅሬታ እንደሚያነሱ የማኅበሩ ፕሬዚዳንት ዮናስ ገልጿል።
በጉባዔው በተለያዩ ምክንያት ከአመራር አባልነት የለቀቁ ሥራ አስፈጻሚዎች እንዲተኩ ከመደረጉም በላይ ቀደም ብሎ ሰባት የነበረው የሥራ አስፈጻሚ አባላት ቁጥር ወደ 11 ከፍ እንዲል ተደርጓል።
ባለፉት አራት ዓመታት የማኅበሩ ፕሬዚዳንት የነበረው ጋዜጠኛ ዮናስ ተሾመ በድጋሜ ተመርጧል።
ጋዜጠኛ መንሱር አብዱልቀኒ፤ ደረጀ ጠገናው እና ቆንጂት ተሾመ በማኅበሩ የሥራ አስፍጻሚነት እንዲቀጥሉ የተወሰነ ሲሆን፤ ፍቅር ይልቃል፣ ሐና ገብረስላሴ፣ ኃይለእግዚብሔር አድሀኖም፣ አርያት ራያ፣ ግርማቸው ከበደ፣ ታደለ አሰፋና ዳግም ዝናቡ አዲሶቹ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባላት ሆነው ተመርጠዋል።