በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ ምድብ “ለ” ላይ የሚሳተፈው የካ ክፍለ ከተማ እግርኳስ ቡድን ሰሞኑን በአንዳንድ የመገናኛ ብዙሃን የውጭ ተጨዋች አስፈረሙ በሚል የሚሰራጨውን ዜና የቡድኑ አሰልጣኝ አስተባብለዋል፡፡
አሰልጣኝ ባንቴ ጌታቸው በተለይም ለሀትሪክ ስፖርት እንደተናገሩት የውጭ ዜግነት ያለው ተጨዋች እንዳስፈረምን ተደርጎ በተወሰኑ የመገናኛ ብዙሃን የሚሰራጨው ዜና ከእውነት የራቀ እና ቡድናቸው የውጭ ተጨዋች የማስፈረም ፍላጎትም ሆነ ዕቅድ የሌላቸው መሆኑን ገልፀዋል፡፡
የካ ክፍለ ከተማ እግርኳስ ቡድን ከታች ያሉ ታዳጊዎች ላይ እየሰራ ያለና መልካም እና አበረታች ውጤቶች እየታዩ በመሆኑ በቀጣይም የማስቀጠል ስራዎች ላይ ትኩረት አድርገው እየሰሩ መሆናቸውን ለሀትሪክ ስፖርት የገለፁት አሰልጣኝ ባንቴ ጌታቸው የውጭ ተጨዋቾች አለማስፈረማቸውንና ከቡድናቸው ጋር የውጭ ተጨዋቾች አለመኖሩንም አረጋግጠዋል፡፡
- ማሰታውቂያ -
የካ ክ/ከተማ እግርኳስ ቡድን የውጭ ዜግነት ያለው ተጨዋች የማስፈረም ፍላጎትም ሆነ ዕቅድ እንደሌላቸው የገለፁት አሰልጣኝ ባንቴ ይሄን ሀሰተኛ ዜና ያሰራጩ የመገናኛ ብዙሃን መጠየቅ ስላለባቸው ተጠያቂ የምናደርግበት ሂደት ላይ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር እየተነጋገሩ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡
የካ ክፍለ ከተማ እግርኳስ ቡድን በከፍተኛ ሊግ ምድብ “ለ” ካደረጓቸው 6 ጨዋታዎች በ5ቱ ተሸንፈው፡በ1ጨዋታ የአቻ ውጤት ሲያስመዘግቡ ምንም ጨዋታ ሳያሸንፉ ፡2ጎል ሲያስቆጥሩ ፡13ጎሎች ተቆጥረውባቸው፡በ11 የግብ ዕዳ 1ቀሪ ተስተካካይ ጨዋታ ኑሯቸው በደረጃ ሰንጠረዡ ግርጌ ላይ ተቀምጠዋል፡፡