የ13ኛ ሳምንት ጨዋታ ዛሬ ጅማሮውን ሲደርግ ነገም ይቀጥላል በዚህም ባህርዳር ከተማ ሰበታ ከተማን የሚያስተናግድበት ጨዋታ የሚከተለውን አቅርበንላችኋል።
ሰበታ ከተማ ከሜዳው ውጪ እጅግ ደካማ ውጤት እያስመዘገበ የሚገኝ ቡድን ሲሆን ሜዳው ላይ (በአዲስ አበባ ስታዲየም) ሲጫወት የተጋጣሚ ቡድን ላይ የጨዋታ ብልጫ የሚወስድ ቡድን ነው። የዘንድሮው የአሰልጣኝ ውበቱ አባተ ሰበታ ከተማ በመስመር በተገደበ የማጥቃት እንቅስቃሴ የሚጫወት ሲሆን አብዛኛውን ጊዜ ለአጥቂዎች ኳስን ለማድረስ የሚጥሩት የመስመር ተከላካዮች እና አማካዮች መሆናቸው ይስተዋላል። ከዚህ በተጨማሪም በነገው ጨዋታ የመሀል ሜዳ ላይ የታደለ መንገሻ፣ መስዑድ መሀመድ እና የዳዊት እስጢፋኖስ ጥምረት እና የጎል ቀበኛው ፍፁም ገ/ማርያም ወደ ግብ አስቆጣሪነት መመለስ በሊጉ በርካታ ግቦች ለሚቆጠሩበት ባህርዳር ከነማ ከባድ ፈተና ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል። በተለይ በግራ ክንፍ የሚጫወተው ባኑ ዲያዋራ ለተከላካዮች ፈታኝ እንደሚሆን ይጠበቃል።
ባለሜዳዎቹ የሚታወቁበት ኳስን ተቆጣጥሮ የመጫወት መንገድ ነገም ተግባራዊ ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። በተለይ የመሀል ሜዳ የኳስ ቁጥጥር ለእንግዳዎቹ ፈታኝ የሚያደርግባቸው ቢሆንም። ሆኖም ግን የጣናው መጎዶች በሜዳቸው ያላቸውን ጥንካሬ እና እንግዳዎቹ ካላቸው የሚዳ ውጭ ጥንካሬ ባለሜዳዎቹ በቀላሉ ነጥብ ሊያገኙ የሚችሉበት አጋጣሚ ቀላል ሊሆን ይችላል ተብሎ ይገመታል። ምንም እንኳ ግብ ለማስቆጠር የማይቸገረው የፊት መስመራቸው ደካማ የመከላከል መስመራቸው ለተጋባዦቹ ቀላል የሚያደርግባቸው ይመስላል። ሰበታ ከተማዎች ከተጋጣሚያቸው ባህርዳር ከነማ በእኩል ነጥብ በ2ግብ ክፍያ ብቻ ተበላልጠው እንደመገኘታቸው የሚያደርጉት ጨዋታ በጉጉት የሚጠበቅ ነው። ይህ ጨዋታ በፀጋው ሽብሩ በዋና ዳኝነት እየመሩት የሚካሄድ ሲሆን በጣናው መጎዶች በኩል አዳማ ሲሰኮ ፣ ማማዱ ሲዲቤ ፤ ፍቅረ ሚካኤል አለሙ ፤ ወሰኑ አሊ እና ሳለአምላክ ተገኝ በጉዳት እና በቅጣት የማይሰለፉ ሲሆን በሰበታ ከተማዎች በኩል ዳዊት እስጢፋኖስ ፤ በኃይሉ አሰፋ ፤ አስቻለው ግርማ የማይሰለፉ ይሆናል። የነገው ጨዋታ ሁለቱም ቡድኖች ሲገናኙ ይህ ለመጀመሪያ ግዜ ነው።