በኑሬ ረጋሳ
በ12ኛው ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የጣናው ሞገድን በሜዳው ያስተናገደው ወልቂጤ ከነማ 2-0 በሆነ ውጤት ማሸነፍ ችሏል።
በሁለቱም ቡድኖች ያማረ የድጋፍ ድባብ የተካሄደው ጨዋታ በባለሜዳዎቹ አሸናፊነት ተጠናቋል። ለወልቂጤ ሁለቱንም ግቦች በሁለተኛው አጋማሽ ተቀይሮ የገባው አህመድ ሁሴን አስቆጥሮ ቡድኑ ሙሉ ሶስት ነጥብ አስጥብቆ እንዲወጣ አስችሎታል፡፡ ተከታታይ ሶስት ጨወታዎችን በማሸነፍ ድል እየተቀናጁ የሚገኙት ክትፎቹ ከባህርዳር በተሻለ ሁኔታ የጨዋታ እንቅስቃሴ አሳይተዋል፡፡
- ማሰታውቂያ -
በደረጃ ሰንጠረዡ 9ኛ ላይ የነበረው ወልቂጤ ከነማ በዛሬው ጨዋታ ጥሩ የሚባል እቅስቃሴ በማሳየትና በርካታ የጎል ሙከራዎች በማድረግ ከባህርዳር ከነማ ተሽለው መገኘት ችለዋል፡፡ በመጀመሪያው የጨዋታ አጋማሽ ባህርዳር ከነማዎች በርካታ ኳሶችን ወደጎል ሙከራ አድርገው የነበረ ቢሆንም ኳስ እና መረብን ግን ማገናኘት አልቻሉም፡፡
በመጀመሪያው የወልቂጤ ከነማው ጫላ ተሸታ ላይ የተሰራውን ጥፋት ተከትሎ የተገኘውን ቅጣት ምት በረኛው ፅዮን መርዕድ በቀላሉ ተቆጣጥሮታል፡፡ ከዚህ በኋላ የረባ ሙከራ ሳይስተዋልበት የመጀመሪያው አጋማሽ ተጠናቋል።
በሁለተኛው አጋማሽ ተጭነው መጫወት የቻሉት ወልቂጤ ከተማዎች ጥረታቸው ፍሬ አፍርቶ 60ኛው ደቂቃ ላይ ከጫላ ተሺታ የተቀበለውን ኳስ አህመድ ሁሴን ወደ ግብነት ቀይሮ ክትፎዎቹን ቀዳሚ ማድረግ ችሏል። ከግቡ መቆጠር በኋላም ጫና መፍጠር የቻሉት ባለሜዳዎቹ ሲሆኑ 88ኛው ደቂቃ ላይ አህመድ ሁሴን ለራሱም ለቡድኑም ሁለተኛ ግብ አስቆጥሮ ቡድኑን አሸናፊ ማድረግ ችሏል።
ውጤቱንም ተከትሎ ወልቂጤ ከተማ ከነበረበት 9ኛ ደረጃ 17ነጥቦችን በመሰብሰብ 5ኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ ባህር ዳር ከነማ በአንፃሩ በእኩል 17ነጥቦች በግብ ክፍያ ተበልጦ ወደ 6ኛ ደረጃ ለመንሸራተት ተገዷል።