የ16ኛ ሳምንት ሁለተኛ ቀን 6ጨዋታዎች ዛሬ (እሁድ) በአዲስ አበባ እና በተለያዩ የክልል ስታዲየሞች ተከናውነዋል። ከነዚህ ጨዋታዎች መካከል ድሬ ስታዲየም ላይ የተደረገው እና ድሬዳዋ ከተማን እና ከሀዋሳ ከተማ ያገናኘው ጨዋታ ተጠቃሽ ሲሆን በጨዋታውም ባለሜዳው ድሬዳዋ ከተማ ጨዋታውን 3-1 በሆነ ውጤት በማሸነፍ የሁለተኛውን ዙር በድል ጀምሯል።
በተጫዋቾች የዝውውር መስኮት 5ተጫዋቾችን አስፈርመው የሁለተኛውን ዙር የጀመሩት ድሬዎች የሁለተኛውን ዙር የመጀመሪያ ጨዋታ በድል ተወጥተዋል። በተደጋጋሚ ጫና መፍጠር የቻሉት እና የሀዋሳ ከተማን ተከላካዮች ሲያስጨንቁ የዋሉት ድሬዳዋ ከተማዎች የመጀመሪያውን ግብ ለማስቆጠር 12ደቂቃዎች ብቻ ነበር የፈጀበት። 12ኛው ደቂቃ ላይ የተገኘዉን ቅጣት ምት የክለቡ አዲስ ፈራሚ ሄኖክ ኢሳያስ ሲያሻማው ሪችሞንድ ኦዶንግ አስቆጥሮ ባለሜዳዎቹን ቀዳሚ ማድረግ ችሏል። ከግቡ መቆጠር በኋላም ድሬዎች ተጨማሪ ግብ ለማግኘት ሀዋሳ ከተማዎች ደግሞ አቻ ለመሆን ጥረት ሲያደርጉ ታይተዋል።
- ማሰታውቂያ -
የመጀመሪያው አጋማሽ ጨዋታ ሊጠናቀቅ 5ደቂቃዎች ሲቀሩት 40ኛው ደቂቃ ላይ በእለቱ ዋና አርቢትር ፌደራል አርቢትር ወልዴ ንዳውና በረዳታቸው መካከል የውሳኔ ልዩነት ተፈጥሮ ታይቷል። ይህም ረዳት ዳኛው የድሬዳዋ ከተማው ኤልያስ ማሞ ፍፁም ቅጣት ምት ክልል ውስጥ ጥፋት ተሰርቶበታል የሚል ምልክት ቢያሳዩም የእለቱ ዋና ዳኛ ደግሞ ጥፋቱ የተሰራው ከፍፁም ቅጣት ምት ሳጥን ውጪ ነው በማለት የተለያየ ውሳኔ ወስነዋል። ሆኖም የእለቱ ዋና ዳኛ በወሰኑት መሰረት የተገኘውን ቅጣት ምት የድሬዳዋ ከተማው ቢንያም ጾመልሳን በቀጥታ መትቶት በግሩም ሁኔታ አስቆጥሮ የባለሜዳዎቹን መሪነት ከፍ ማድረግ ችሏል። በዚህም የመጀመሪያው አጋማሽ በድሬዳዋ ከተማ 2-0 መሪነት ተጠናቋል።
በሁለተኛው ዙር የመጀመሪያ ሳምንት ጠንክረው የቀረቡት ድሬዳዋዎች በሁለተኛው የጨዋታ አጋማሽም ጠንክረው ሲሰሩ ታይተዋል። ሁለተኛው አጋማሽ ከተጀመረ 8ደቂቃዎች በኋላ 53ኛው ደቂቃ ላይ የድሬዳዋ ከተማው አማረ በቀለ በድንቅ ሁኔታ ተከላካዮችን አልፎ ያሻገረለትን ኳስ ቢንያም ጾመልሳን በድንቅ ሁኔታ ጨርሶ ለራሱ ሁለተኛውን ለቡድኑ ደግሞ 3ኛውን ግብ ማስቆጠር ይቻላል። ጨዋታው ሊጠናቀቅ 3ደቂቃዎች ሲቀሩት 87ኛው ደቂቃ ላይ የሀዋሳ ከተማው መስፍን ታፈሰ እንግዳዎቹን ከባዶ መሸነፍ የታደገችውን ግብ አስቆጥሯል።
ውጤቱንም ተከትሎ ድሬዳዋ ከተማ 20 ነጥቦችን በመሰብሰብ 11ኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ ሀዋሳ ከተማ በበኩሉ በ22 ነጥቦች ወደ 7ኛ ደረጃ ለመንሸራተት ተገዷል።
📷 © dire kemema page