13ኛው የአዲስ አበባ ከተማ ዋንጫ ዕጣ ማውጣት ዛሬ በኢትዮጵያ ሆቴል የተካሄደ ሲሆን ከመስከረም 26 -ጥቅምት 11 2011ዓ.ም በሚካሄደው በዚህ ውድድር ተሳታፊ ክለቦች ተጋጣሚዎቻቸውን አውቀዋል።
የአ/አ እግርኳስ ፌደሬሽን ፕሬዚዳንት ኢ/ር ኃይለየሱስ ፍስሃ ስለውድድሩ ማብራሪያ ሰጥተዋል። ውድድሩ ከመስከረም 26 – ጥቅምት 11 2011ዓ.ም እንደሚካሄድ እቅድ የያዝን ቢሆንም የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌደሬሽን ውድድሩን እስከ ጥቅምት 7 ድረስ እንድናጠናቅቅ ነግሮናል ነገር ግን በተባልነው ጊዜ ማጠናቀቅ አንችልም ብለዋል።
ስለውድድሩ አሸናፊ ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ ኢ/ር ኃይለየሱስ ፍስሀ “አምና በተሻሻለው ህገደምብ መሰረት የክልል ክለቦች ውድድሩን ሲያሸንፉ ዋናው ዋንጫ እንደሚሰጣቸው ተናግረዋል። ከዋንጫው ሽልማት በተጨማሪ የክልል ተጋባዥ ክለቦች እንደየ ደረጃቸው ከሚገኘው ጠቅላላ ገቢ በፐርሰንት እንደሚሰጣቸው ተገልጿል። ይህንንም ተከትሎ አሸናፊ ለሚሆነው ክለብ 15%፣ ለዋንጫ ተፎካካሪ ክለብ 10%፣ ሶስተኛ ለሚወጣው 7%፣ አራተኛ ለሚወጣው 4% እንዲሁም ቀሪዎቹ በየደረጃቸው 3% ለየክለቦቹ እንደሚሰጥ ተብራርቷል።
በመጨረሻም የውድድሩ ዕጣ ማውጣት ስነስርዓት የተካሄደ ሲሆን 8ክለቦች በሁለት ምድብ ተከፍለው የሚደረግ ይሆናል። ከጊዜ ወደጊዜ የአ/አ ቡድኖች እያነሱ የመጡበት ይህ ውድድር ከከተማዋ 3ክለቦች ብቻ ተሳታፊ ሲሆኑ ቀሪዎቹ 5ቡድኖች ተጋባዦች እንዲሆኑ አስገድዷል።
- ማሰታውቂያ -
በዚህም መሰረት ኢትዮጵያ ቡና እና ፋሲል ከተማ የሁለቱ ምድቦች የምድብ አባት ሆነው ተመርጠዋል።
ምድብ ሀ
ኢትዮጵያ ቡና
መከላከያ
ኢትዮ ኤሌክትሪክ
አዳማ ከተማ
ምድብ ለ
ፋሲል ከነማ
ወላይታ ድቻ
ኳራ ዩናይትድ(ከናይጄሪያ)
ጅማ አባጅፋር
ወድድሩ ቅዳሜ መስከረም 26 8:00 መከላከያ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ 10:00 ደግሞ አዳማ ከተማ ከኢትዮጵያ ቡና በሚያደርጉት ጨዋታ ውድድሩ የሚጀመር ይሆናል። ከዚህም ጋር ተያይዞ የስታዲየም መግቢያ ዋጋዎች የታወቀ ሲሆን ክቡር ትሪቡን 250 ብር ጥላ ፎቅ 120ብር ከማን አንሼ በወንበር 70ብር ከማን አንሼ ያለ ወንበር 50ብር ካታንጋ 30ብር እንዲሁም ዳፍ ትራክ እና ሚስማር ተራ 15 ብር እንደሚሆኑ ተገልጿል።