በአምናው የዉድድር አመት ከከፍተኛ ሊጉ ምድብ ለ የቀዳሚነት ደረጃን በመያዝ ወደ ሊጉ መቀላቀል የቻሉት አዲስአበባ ከተማዎች አስከፊ ከነበረው የሊጉ አጀማመራቸዉ ለየት ያለ ሳምንትን አሳልፈዋል።
ገና ከሊጉ ጅማሮ አስቀድሞ በ15ኛዉ የአዲስአበባ ከተማ ዋንጫ ላይ መሳተፍ የቻሉት አዲስአበባ ከተማዎች በምድባቸዉ ያደረጓቸውን ስስቱንም ጨዋታዎች ተሸንፈው አንድም ግብ ማስቆጠር ሳይችሉ ከዉድድሩ ዉጭ መሆናቸዉ ይታወሳል። ይሄንንም ተከትሎ አስከፊ የዉድድር አመትን ያሳልፋሉ ተብሎ በብዙዎች ዘንድ ግምት ተሰጥቷቸው የነበሩት አዲስአበባ ከተማዎች በሲቲ ካፑ ላይ ባስመዘገቡት ዉጤት ብቻ ሳይሆን በዝዉዉር ገበያው ላይ በንቃት ተሳትፎ አለማድረጋቸዉም ተጠቃሽ ነዉ።
በዚህ ዙሪያ ተደጋጋሚ ጊዜ ጥያቄ ሲቀርብላቸው የነበሩት የቡድኑ ዋና አሰልጣኝ እስማኤል አቡበከር ምንም እንኳን በጊዜያዊነት ከሀላፊነት ቢታገዱም የሚከተለዉን ሀሳብ ሲሰጡ ይስተዋላሉ ቡድናቸዉ ከሁሉም የፕሪሚየር ሊግ ክለቦች ዘግይቶ ወደ ቅድመ ዉድድር ዝግጅት መግባቱ ፣ የአዲስአበባ ከተማ ዋንጫ ላይ ለመሳተፍ ሲመጡ ልምምድ ከጀመሩ ገና ሁለት ሳምንታቸዉ እንደነበር በዚህም እንደዚያ አይነት የወረደ ዉጤት ሊመዘገብ መቻሉን እና በፈለጉት መንገድ የሚፈልጓቸዉን ተጫዋቾች ማስፈረም አለመቻላቸዉ ተፅዕኖ እንደሚኖረዉ ነገር ግን እንደምንም በሊጉ ለመቆየት ጥረት እንደሚያደርጉ ሲገልፁ ተስተውሏል።
የሊጉን የመጀመሪያ ሁለት ሳምንታት በተከታታይ የተሸነፉት አዲስአበባ ከተማዎች በሶስተኛው ሳምንት ደግሞ አዲስ አዳጊዉን መከላከያ ሶስት ለዜሮ በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችለዋል። ያለ ዋና አሰልጣኛቸው እስማኤል አቡበከር በምክትል አሰልጣኛቸው ደምሰው ፍቃዱ እየተመሩ ወደ ሜዳ የገቡት አዲስአበባዎች በፍፁም ጥላሁን ሁለት እና ሮቤል ግርማ ባስቆጠሩዋቸዉ ሶስት ጎሎች ተጋጣሚያቸውን በመርታት በሊጉ የመጀመሪያ ሶስት ነጥባቸዉን ሲያሳኩ በደረጃ ሰንጠረዡም 11ኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ችለዋል። ይሄ ድልም ለቀጣይ ለሚያደርጓቸዉ ጨዋታዎች ጥሩ የመነሳሳት መንፈስን እንደሚፈጥርላቸው ይጠበቃል።