የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የዲሲፕሊን ኮሚቴ አዳማ ከተማ ምንተስኖት አዳነን ወደ ስራው እንዲመልስ አዘዘ።
ዲሲፕሊን ኮሚቴው ተጨዋቹ ከክለቡ የታገደበትን ውሳኔ በመቃወም ፍትህ እንዲሰጠው ያቀረበውን ክስ ከተመለከተ በኋላ ክለቡ በተመሳሳይ ለዲሲፕሊን ኮሚቴ የሰጠውን ምላሽ ሲመረምር ቆይቷል። ክለቡ በሰጠው ምላሽ ተጨዋቹ ከልምምድ ቀርቷል በሲቲ ካፑ የቅዱስ ጊዮርጊስ መለያ በመሳም ደጋፊው እንዲረብሽ አድርጓል ተደጋጋሚ ጊዜ ቢጠራም ወደ ክለቡ አልመለስም በማለቱ ተጨዋቹን አግደን ሌላ ተጨዋች በቦታው እንድናስፈርም የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽንን ጠይቀናል በማለት የሰጠውን ምላሽ በመመልከት የአዳማ ከተማን ጥያቄ ውድቅ አድርጓል።
ኮሚቴውም የሁለቱን ወገኖች ምላሽ ከመረመረ በኋላ አዳማ ከተማ በአስቸኳይ ተጨዋቹን ወደ ክለቡ እንዲመልስ፣ ከህዳር ወር ጀምሮ አሁን የሚመለስበት ድረስ ያለውን ደመወዝ እንዲከፍል፣ ውሳኔው በደረሰው ሰባት ቀን ውስጥ ተግባራዊ እንዲያደርግ፣ ይህ የማይሆን ከሆነ ከስምንተኛው ቀን ጀምሮ በየቀኑ 2 በመቶ መቀጫ እንዲከፍል ከፌዴሬሽኑ ግልጋሎት እንዳያገኝና ከፕሪሚየር ሊጉ ውድድር እንዲታገድ መወሰኑን አስታውቋል። ኮሚቴው የክለቡ ይግባኝ የማለት መብት በህግ የተጠበቀ መሆኑን አስታውቋል።
ክለቡ ተጨዋቹ ወደ ልምምድ መጥቶ አያውቅም ቢልም ተጨዋቹ ከ25/3/2014 እስከ 9/4/2014 ድረስ በክለቡ ተጨዋቾች መመገቢያ መዝገብ ተራ ቁጥር 19 ላይ ተመዝግቦ መገኘቱ የክለቡ ተጨዋቹ ወደ ክለቡ አልተመለሰምን ክስ ውድቅ እንዲያደርግ ማስቻሉን ኮሚቴው አስረድቷል።
የሁለቱ ወገኖች ክርክር ከእግርኳሳዊ ውጪ ወደ መደበኛ ፍርድ ቤትም መሄዱ የታወቀ ሲሆን የፍርድ ቤቱ ውሳኔም እየተጠበቀ ነው።