በዕለተ ቅዳሜ መስከረም 14/2014 ዓ.ም ጅማሮዉን ያደረገዉ የአዲስአበባ ከተማ ዋንጫ በዛሬዉ ዕለትም ቀጥሎ ሲካሄድ ቀን 8:00 ሰዓት ላይ ባህርዳር ከተማን ከ አዳማ ከተማ የሚያገናኝ ሲሆን አመሻሽ 10:00 ሰዓት ላይ ደግሞ የአምናዉን የሊጉ ሻምፒዮን ፋሲል ከነማ ከ ቅዱስ ጊዮርጊስ የሚያገናኝ ይሆናል።
በአበበ በቂላ ስታዲየም በሚከናወነው ዉድድርም ከረዥም ጊዜ በኋላ ማለትም ከአንድ አመት ከስድስት ወራት ቆይታ በኋላ ደጋፊዎች በስታዲየም ተገኝተዉ ጨዋታዎችን መታደም የሚችሉ ሲሆን በዉድድሩ የመክፈቻ ጨዋታ ቀንም 10:00 ላይ የተካሄደዉን የኢትዮጵያ ቡና እና ጅማ አባጅፋር ጨዋታ ለመመልከት በርከት ያሉ ደጋፊዎች በስታዲየሙ ተገኘተው ባማረ ድባብ ክለባቸዉን ሲያበረታቱ ተመልክተናል።
በመክፈቻው ጨዋታም ዘንድሮ ወደ ሊጉ የተመለሱት ሁለቱ የመዲናዋ ክለቦች አዲስአበባ ከተማ እና መከላከያ ተጫዉተዉ መከላከያ በቢንያም በላይ ሁለት ግቦች ታግዞ ሁለት ለዜሮ አሸንፎ መዉጣት ችሏል። በዕለቱ ሁለተኛ ጨዋታም ኢትዮጵያ ቡና በጅማ አባጅፋር በተመሳሳይ ሁለት ለዜሮ ተሸንፏል። በዚህ መሰረትም ምድብ አንድን መከላከያ እና ጅማ አባጅፋር በተመሳሳይ ሶስት ነጥብ እና ንፁህ ሁለት ጎል መምራት ጀምረዋል።
በዛሬዉ ተጠባቂ ጨዋታም አብዝሀኛዎቹን ተጫዋቾች ለብሔራዊ ቡድን ግዳጅ የላከዉ ፋሲል ከነማ በተመሳሳይ በክረምቱ የተጫዋቾች የዝዉዉር መስኮት በርከት ያሉ ተጫዋቾችን ካስፈረሙት ፈረሰኞቹ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ሲሆን ከዚህ ቀደም ብሎም 8:00 ሰዓት ላይ ባህርዳር ከተማዎች በቀድሞ አሰልጣኛቸዉ የሚሰለጥኑትን አዳማ ከተማዎች የሚገጥሙ ይሆናል።
- ማሰታውቂያ -
በዉድድሩም በየጨዋታው ኮከብ ሆነዉ ለሚመረጡ ተጫዋቾች የአስራ ሁለት ሺህ ብር እና የዋንጫ ሽልማት ከጨዋታዉ መጠናቀቅ በኋላ የሚበረከትላቸዉ ይሆናል።