የቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 5ኛ ሳምንት በተደረጉ ስምንት ጨዋታዎች ስድስት ጨዋታዎች በመሸናነፍ ሁለት ጨዋታ ደግሞ በአቻ ሲጠናቀቁ በአጠቃላይ 18 ጎሎች ተቆጥረዋል ።
አንድ የ3ኛ ሳምንት ተስተካካይ ጨዋታ ያለምንም ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል።
በሳምንቱ 58 ተጫዋቾችና የቡድን አመራሮች በቢጫ ካርድ ሲገሰፁ አንድ ተጫዋች በሁለተኛ ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ውድድር አመራርና ስነ-ስርዓት ኮሚቴ ጥቅምት 20/2015 ዓ.ም ባደረገው ስብሰባ በሳምንቱ በተደረጉ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ግጥሚያ(ዎች) ከዳኞች እና ከታዛቢዎች የቀረቡለትን የዲሲፕሊን ሪፖርት ከመረመረ በኋላ የተለያዩ ውሳኔዎችን አስተላልፏል።
- ማሰታውቂያ -
በተጫዋቾች ደረጃ ኩሊባሊ ከድር (ፋሲል ከነማ) ከስፖርታዊ ጨዋነት ውጭ በመጫወቱ ከጨዋታ ሜዳ የተወገደ ስለመሆኑ ሪፖርት የቀረበበት ስለሆነ በኢ.እ.ፌ ዲሲፕሊን መመሪያ መሰረት 1 ጨዋታ እንዲታገድና በተጨማሪ የገንዘብ ቅጣት ብር 1500 /አንድ ሺ አምስት መቶ/ እንዲከፍል ተወስኗል።
በክለቦች መቻል ፤ ድሬደዋ ከተማ ፤ ሲዳማ ቡና ፤ ፋሲል ከነማ ፤ ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ወላይታ ድቻ የየክለባቸው አምስት እና ከዛ በላይ ተጫዋቾች በተለያዩ ጥፋቶች ካርድ የተሰጣቸው በመሆኑ በኢ.እ.ፌ ዲሲፕሊን መመሪያ መሰረት እያንዳንዳቸው የገንዘብ ቅጣት ብር 5000 /አምስት ሺ/ እንዲከፍሉ እንዲሁም ቅዱስ ጊዮርጊስ ከፋሲል ከነማ ጋር ባደረገው ጨዋታ የክለቡ ደጋፊዎች የእለቱን ዳኛ አፀያፊ ስድብ ስለመሳደባቸው ሪፖርት የቀረበበት በመሆኑ ደጋፊዎቹ በፈጸሙት ጥፋት ክለቡ በኢ.እ.ፌ ዲሲፕሊን መመሪያ መሰረት ብር 50,000/ሃምሳ ሺህ/ እንዲከፍል ተወስኗል፡፡