የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ አክሲዮን ማህበር የ2014 ዓ.ም የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግን ጥቅምት 7/2014 ለመጀመር ቅድመ ዝግጅት እያደረገ እንደሚገኝ ይታወቃል።
የዝግጅቱ አንድ አካል የሆነው የእጣ አወጣጥ ስነ-ስርአትም በዛሬው ዕለት ከቀኑ 8:30 ሰአት የሊጉ ተሳታፊ ክለብ ተወካዮች በተገኙበት ተካሂዷል።
የሊግ ካምፓኒው ሰብሳቢ መቶ አለቃ ፈቃደ ማሞ በቀጣዩ የውድድር ዓመት የተሻለ ነገር እንዲገጥማቸዉ ምኞታቸውን በመግለፅ የእጣ አወጣጥ ስነስርዓቱን በይፋ አስጀምረዋል።
- ማሰታውቂያ -
ከመቶ አለቃ የመክፈቻ ንግግር በፊትም በዕለቱ የእጣ ማዉጣት ስነ-ስርዐቱ የሚካሄድበትን የአክሲዮን ማህበሩ አዲስ ቢሮ በይፋ በስፍራው ለነበሩ እንግዶች ተዋዉቋል።
በዕለቱም የዉድድር አመቱ የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ የነበረዉ እና የዕለቱ የክብር ዕንግዳ አቡበከር ናስር በስፍራዉ ተገኝቶ ከአክሲዮን ማህበሩ ስራ አስኪያጅ አቶ ክፍሌ ሰይፈ ጋር በመሆን በጋራ ዕጣዉን ማዉጣት ችለዋል።
ካለፈዉ የዉድድር አመት ተሻሽሎ በ16 ክለቦች መካከል በሚከወነዉ የ2014 አመት የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ዉድድር በመጀመሪያው ሳምንት ጨዋታም፦
አርባምንጭ ከተማ ከ መከላከያ
ባህር ዳር ከተማ ከ አ.አ ከተማ
ፋሲል ከነማ ከ ሀድያ ሆሳዕና
አዳማ ከተማ ከ ወልቂጤ ከተማ
ሀዋሳ ከተማ ከ ጅማ አባ ጅፋር
ድሬደዋ ከተማ ከ ወላይታ ድቻ
ኢትዮጵያ ቡና ከ ሲዳማ ቡና
ሰበታ ከተማ ከ ቅዱስ ጊዮርጊስ
የሚያገናኝ ይሆናል ።
በተጨማሪም በጉጉት የሚጠበቀዉ የሁለቱ የመዲናዋ ክለቦች ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ኢትዮጵያ ቡና የሚያደርጉት ተጠባቂው የሸገር ደርቢ ጨዋታ በሁለተኛው ሳምንት ላይ እንደሚደረግ ታዉቋል።
በተያያዘም በዛሬዉ ዕለት የእጣ ማዉጣት ስነስርዓቱ የተከናወነዉ የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ መርሐ ግብር የቀናት ለዉጥ ሊደረግበት የሚችለዉ በሚከተሉት ምክንያቶች ብቻ እንደሆነ የዉድድር እና ስነስርዓት ኮሚቴ ሰብሳቢ የሆኑት ዶ/ር ወገኔ ዋልተንጉስ ገልፀዋል።
1. የብሔራዊ ቡድን ጨዋታዎች ላይ የቀን ለውጥ ከተደረገ፤
2. በአፍሪካ ዋንጫ ላይ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከውድድሩ አስቀድሞ ከተሰናበተ፤
• ይህ የሚሆን ከሆነ ቡድኑ ወደ ኢትዮጵያ በተመለሰ በአምስተኛ ቀኑ ውድድር ይጀምራል ።
3. ብሔራዊ ቡድኑ የ3ኛ ዙር የአለም ዋንጫ ማጣርያ ጥሎ ማለፍ ውድድር ካለፈ፤
• ውድድሮች ቢያንስ ለ አስራ ዘጠኝ ቀናት የሚቋረጡ ይሆናል ።