“እኔን የፈለጉኝ የሀድያ ሆሳዕና ደጋፊዎች እንጂ አመራሮቹ አይደሉም”
“አሰልጣኝ ውበቱ ፍላጎቱ ካለህና ፍቃደኛ ከሆንክ መቀጠል ትችላለህ ብሎኝ ነበር”
“ለሃዲያ ሆሳዕና ያልፈረምኩት ቦርዱ አልተሟላም ብለው መልሰውኝ ነው”
” የሲዳማ ቡና ተጨዋቾችና አሰልጣኞቹ እንደቆየሁበት ክለብ እንዲሰማኝ አድርገውኛል”
- ማሰታውቂያ -
በዛብህ መለዮ
/ሲዳማ ቡና/
ባለፉት አምስት አመታት የፕሪሚየር ሊጉ፣ የጥሎማለፍና የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫን አንስቶ ከአጼዎቹ ጋር በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒየንስ ሊግና በኮንፌዴሬሽን ካፕ ኢትዮጵያን የመወከል ውጤታማ ታሪክ ከስቷል…. በዛብህ መለዮ…. አሁን ግን ይሄ ታሪክ ሆኗል ተጨዋቹ ከአጼዎቹ መንደር ተሰናብቶ በቀድሞ አሰልጣኙ ስዩም ከበደ ጥላ ውስጥ ገብቷል…. በዛብህ ፊርማውን ለሲዳማ ቡና ካኖረ በኋላ ጠዋት ላይ ማሊያውን ይዞ የፎቶ መነሳት የትውውቅ ስነስርዓት ተካሄደ። በዛው ቀን ከሰአታት ቆይታ ሱዳማ ቡና ከኪንዳ ቦይስ ጋር ባደረገው የሲዳማ ካፕ ላይ ተሳተፈ። ከፋሲል ከነማ መልቀቁ ባይቀርም ከነሱ ጋር ልምምድ ሲሰራ የነበረውን በዛብህን አሰልጣኝ ስዩም ከበደ ቀይሮ አስገባው… አሰልጣኙን አላሳፈረውም ዝውውሩ ምርጥ መሆኑንም ባስመሰከረበት ጨዋታ ሁለት ግብ የሆኑ ኳሶችን ሲያቀብል አንድ የፍጹም ቅጣት ምት አስገኘ አንድ ግብ አስቆጠረ ይሄ ደግሞ የሲዳማ ቡና ደጋፊዎችን አስጨፈረ….. ይሄ ድንቅ ጅማሮ ያስተዋለው የሀትሪክ ድረገጹ ባልደረባ ዮሴፍ ከፈለኝ እንዴት ፋሲል ከነማዎች ለቀቁት፣ ሌሎች ክለቦችስ ለምን አልፈለጉትም፣ የአሰልጣኝ ውበቱ አባተ ትኩረት ለምን ተነፈገው፣ ቀጣይ እቅዱ ምን ይሆን በሚልና ሌሎች ጥያቄዎችን ይዞ ከተጨዋቹ ጋር ያደረገው ቆይታ ይህን ይመስላል….
በሀትሪክ:- ሲዳማ ቡናን ከተቀላቀልክ ሁለተኛ ቀንህ ነው አስገራሚ አጀማመር አደረክ … ምን ተሰማህ…?
በዛብህ:- እውነት ነው ሁለተኛ ቀኔን ይዣለሁ…አሪፍ ክለብ ነው በሁለት ቀን ውስጥ በሲዳማ ሲቲ ካፕ ላይም ተጫውቼ አሪፍ አጀማመር በማድረጌ ደስ ብሎኛል በራስ መተማመኔን ጨምሮልኛል አብሬ ልምምድ የሰራሁ ነው የሚመስለው ተጨዋቾቹም ጥሩ ተቀብለውኛል ነገሮች ቀለል እንዲል ያደረገልኝ እሱ ነው በዚህ አጋጣሚ ሁሉንም አመሰግናለሁ
ሀትሪክ:- ሲዳማ ቡናን የመረጥከው የመጫወት ፍላጎት ስለነበረህ ነው..? ወይስ የተሻለ ጥቅማ ጥቅም ስላቀረበልህ..?
በዛብህ:- ለሃዲያ ሆሳዕና የመጫወት ፍላጎት ነበር የነበረኝ …የተወለድኩበት የተነሳሁበትም አካባቢዬ ነው ብዙ ለመሄድም የሞከርኩትም ለዚህ ነበር ግን አልሆነም… ለካ እኔ እንድጫወት ፍላጎት የነበረው ደጋፊዎች ጋር ነበር…ደጋፊው ብዙ ጊዜ ፈልጎኝ መገጣጠም አልቻልንም ነበር ዘንድሮ ግን ዕድሉ ስለነበር አመራሮቹ ጠርተውኝ በአል ሳላከብር ሁሉ እዚያ ድረስ ሄጄ ቦርዱ አልተሟላም በሚል መልሰውኛል። ደጋፊውን አከብራለሁ እኔን የፈለጉኝ የሀድያ ሆሳዕና ደጋፊዎች እንጂ አመራሮቹ አይደሉም …የሚሰማኝ እንዲህ ነውው ብዬ አላምንም። የደጋፊውን ስሜት ያለመሟላቱ ምክንያት ይሄ መሆኑን መናገር እፈልጋለሁ…. በዓል ሳላከብርም ሄጄ ለሃዲያ ሆሳዕና ያልፈረምኩት ቦርዱ አልተሟላም ብለው መልሰውኝ መሆኑን ደጋፊው እንዲያውቅልኝ እፈልጋለሁ።
ሀትሪክ:- ከዚያ ምን ተፈጠረ..?
በዛብህ:- በዚህ መሃል ሲዳማ ቡና ጥያቄ አቅርቦልኝ ለመግባባት ችያለሁ.. አመራሮቹ ከሀድያ ሆሳዕና አመራሮች በተለየ መንገድ ፈልገውኝ ሊቀበሉኝ ሲጥሩ ሳይ በመፈላለግ ውስጥ በመሆናችን ለመስማማት አልከበደንም ሁለቱም ወገኖች ካልተፈላለጉ እንደማይቻል ያየሁበት ገጠመኝ ነው።
ሀትሪክ:- በሲዳማ ቡና መፈለግህ ምን ስሜት ፈጠረልህ….?
በዛብህ:- ከሲዳማ ቡናዎች ለኛ ፈርምልን የሚለው ጥያቄ ሲቀርብልኝ በደስታ ነው የተቀበልኩት… ደጋፊው ደስ የሚል ነው አሪፍ አቀባበል ነው ያደረጉልኝ.. ዋና ስራ አስኪያጁ አቶ አቡሽ ‘በርግጥ አሁንም ትልቅ ነህ ግን ትላንት የነበረውን በዛብህን ከዚያም የተሻለውን ትልቅ ተጨዋች እናደርግሃለን ይህንን አምናለሁ’ ብሎ ነው ያስፈረመኝ… ይሄ ትልቅ ደስታ ፈጥሮልኛል። ለሲዳማ ቡና የምችለውን ለማድረግም ተዘጋጅቻለሁ
ሀትሪክ:- ከፋሲል ከተማ ጋር የተለያችሁት በስምምነት ነው የሚል መረጃ አገኘሁ…እውነት ነው…?
በዛብህ:- አዎ …የ2016 ኮንትራት ነበረኝ… ክረምት ላይ በስምምነት እንለያይ ብለው ጥያቄ አቀረቡልኝ… ለምን ስላቸው በ2016 ዕቅዳችን ውስጥ የለህም የወሰድከውን የቅድመ ክፍያ ግማሹን ብር መልስና እንለያይ ብለው ጠየቁኝ ተስማምቼ መልሼላቸው ተለያየን። በርግጥ ውል ስላለኝ መቆየት ብፈልግም ሳልፈለግ መቆየትንም አልመረጥኩም ። እግር ኳስ መጫወት ስለምፈልግ ለሚፈልገኝ ሲዳማ ቡና ፈርሜያለሁ።
ሀትሪክ:- ስሜትህ አልተጎዳም..?
በዛብህ:- ፋሲል ከነማ አምስት አመት ሙሉ የተጫወትኩበት ክለብ ነው። መለያየቱ ከነሱም ቢመጣ እግርኳስ ለመጫወት ስል ለቅቄያለሁ… ትንሽ ቅር ያለኝ በዚህ መንገድ መውጣት አልፈለኩም ነበር … የምወደውን ደጋፊ የመሰናበት ዕድል የማላገኝበት ሁኔታ ተፈጥሮ ስለወጣሁ በዚህ አጋጣሚ ማመስገን እፈልጋለሁ ከልብ የመነጨ ምስጋናዬ ይድረሳችሁ። እግርኳስ የትና መቼ እንደሚያገናኝህ አታውቀውምና… የፋሲል ከነማ ደጋፊ ለክለቡ ሲል ራሱን የሚሰዋ በመሆኑ በዚህ መልኩ ባልሰናበትና ባልወጣ ደስ ይለኝ ነበር ግን አልሆነም… እኛ አካባቢ ላይ እግርኳስ ውለታ የለውም የሚለው አባባል ጭምር ተነግሮኛልና መጥፎም መልካምም ጊዜ አሳልፈናልና ለነበረኝ ጊዜ አመሰግናለሁ
ሀትሪክ:- አሰልጣኝ ውበቱ አባተስ ከተሾመ በኋላ ሊያስቀርህ አልሞከረም..? ወይስ አልተገናኛችሁም..?
በዛብህ:- የአሰልጣኙና የክለቡ ቀጣይ ዕቅድ ውስጥ ከሌሉ ተጨዋቾች መሃል አንዱ ነህ በስምምነት እንለያይ ብሎ ያነጋገረኝ የክለቡ ቦርድ ነው…. በወቅቱ በጉዳት ምክንያት ወደ አራት ጨዋታ አምልጦኝ ነበር አዲሱ የውድድር አመት ዝግጅት ከተጀመረ ከ10 ቀን በኋላ ነው ወደ ዝግጅት የገባሁት…እንደማልቀጥል ስለተነገረኝም ነው የዘገየሁት… ወደ ዝግጅት ከገባሁ በኋላ ነው ከአሰልጣኝ ውበቱ አባተ ጋር የተገናኘሁትና በጥሩ ሁኔታ ስለሰራሁ ፍላጎቱ ካለህና ፍቃደኛ ከሆንክ መቀጠል ትችላለህ ብሎኝ ነበር እኔ ግን ስለወሰንኩና የሚጠበቀውን ሁሉ ስላዘገሰጀሁ ሃሳቤን ሳልቀይር ወጥቻለሁ… በሌላ አጋጣሚ ከሱ ጋር መስራት እንደምንችንል አውርተን በጥሩ መንፈስ ነው ከአሰልጣኙ ጋር የተለያየነው እሱ ያለኝ ነገሮች ነበሩ እነሱን አስተካክዬ በሌላ ጊዜ አብሬው ልሰራ እንደምንችልም አውርተን ተለያይተናል…
ሀትሪክ:- ሲዳማ ቡናን ያለፉትን 5 አመታት ታላቅ ስኬት የያዘውን ኮከብ ነው ያስፈረማችሁት ማለት ይቻላል
በዛብህ:- እንግዲህ እሱ ወደፊት የሚታወቅ ነው/ሳቅ/ ከዚህ በኋላ ለማሳየው አቋም ነው የምዘጋጀው ከሲዳማ ቡና ጋር ስለማሳካው ድልና ስለሚመዘገበው ውጤት ነው የማስበው….
ሀትሪክ:- የሲዳማ ቡና ስብስብ ተመቸህ..? ውጤታማ የሚሆን ይመስልሃል…?
በዛብህ:- በደንብ…ስብስቡም ተመችቶኛል…. ትላንት አብሮኝ ሻምፒዮን የሆነ አሰልጣኜ እዚህ ቡድን ውስጥ አለ…ጥሩ ጥሩ ተጨዋቾች አሉበት ..አሪፍ የጨዋታ መንገድን ይከተላል…ተጨዋቾቹና የአሰልጣኞቹ ስብስብ እንደቆየሁበት ክለብ እንዲሰማኝ ነው አድርገውኛልና ነጻ ሆኜ የምጫወት ይሆናል እነሱንም አመሰግናለሁ…..
ሀትሪክ:- የጎፈሬ ሲዳማ ካፕን ተከታትለሃል..?
በዛብህ:- ከፋሲል ከነማ ጋር ዝግጅት እየሰራሁ ቆይቻለሁ በጎፈሬ ሲዳማ ካፕም አልተካፈልኩም ፋሲል ከነማና ሲዳማ ቡና ሲጫወቱ ከፋሲል ከነማ ጋር የነበረኝን ውል ለመቅደድ አዲስ አበባ ወደሚገኘው የፌዴሬሽኑ ጽ/ቤት ሄጄ ስለነበር አላየሁትም…
ሀትሪክ:- የመጨረሻ ጥያቄ ለአዲሱ ክለብህ አመራሮችና ደጋፊዎች የምትለው ካለ….?
በዛብህ:- አምነው ስላስፈረሙኝ ማመስገን እፈልጋለሁ የቡድኑ አመራሮች፣ አሰልጣኞችነና ደጋፊዎች ከነለ የሚፈልጉት ነገር አለ ያንን ደግሞ በርግጠኝነት እንደማደርገው አረጋግጥላቸዋለሁ ለቡድኑ ውጤት የተቻለኝን አቅሜ የፈቀደውን ሁሉ ለማድረግ ተዘጋጅቻለሁ…ደጋፊዎቹም አሪፎች ናቸው እንደ ሁሌውም ከእኛ ጎን እንዲቆሙ ጥሪ አደርጋለሁ። ከዚያ ውጪ ያን ሁሉ ውጤታማ ጊዜ ያሳለፍኩበትን የፋሲል ከነማ ደጋፊዎችንም ከልብ አመሰግናለሁ።