የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ2014 መርሃ ግብር ሊጀመር አራት ቀናት በቀረበት በአሁኑ ወቅት የኮቪድ 19 ምርመራ ሂደት ክርክር ፈጥሯል።
ሊግ ኩባንያው ከ16ቱ ክለቦች ተወካዮች ጋር ዛሬ ባደረገው ውይይት ላይ አንዱ መነጋገርያ ርዕስ የነበረው የኮቪድ 19 ጉዳይ ነው። የኩባንያው አመራሮች የኮቪድ 19 ክትባት ያለውን ጥቅም በህክምና ባለሙያ ማብራሪያ እንዲሰጥ ካደረጉ እሁድ በሚጀመረው ፕሪሚየር ሊግ ከጨዋታ በፊት የ72 ሰአት የምርመራ ውጤት ማምጣቱ የግድ መሆኑን አሳስበዋል።በክትባቱ ጥቅም ርግጠኞች ነን የተከተበ ሰው ቢያንስ ጉዳት አይደርስበትም ቫይረሱን የመቋቋም አቅም ይኖረዋል በማለት ምክራቸውንም ለግሰዋል።
የሊግ ኩባንያው አመራሮች ለክለቦቹ በሰጡት ማሳሰቢያ “በኛ በኩል አስገዳጅ ያደረግነው የ72 ሰአት የኮቪድ 19 ምርመራ ውጤትን እንጂ ክትባትን አይደለም በተፈቀደላቸውና ዕውቅና ባላቸው ተቋማት ምርመራ መውሰድና ኔጌቲቭ መሆናቸውን ማረጋገጥ ግን ይጠበቅባችዋል” በማለት ማሳሰቢያ ሰጥቷል።
በሌላ በኩል ከ1-3 ለወጡ ክለቦች የሚሰጠው ሜዳሊያ ቁጥር ወደ 42 ከፍ ማለቱ ተሰምቷል። ከዚህ በፊት የነበረው የ35 አባላት/ 25 ተጨዋቾች፣ 5 ከወጣት ቡድን ላደጉ፣ 5 አሰልጣኞች/ ይሰጥ የነበረው የወርቅ የብርና የነሃስ ሜዳሊያዎች ቁጥር መጨመሩ ታውቋል። ስምምነት በተደረሰው አዲሱ ውሳኔ ለ25 ተጨዋቾች ከተስፋ ቡድን ላደጉ 10 ተጨማሪ ተጨዋቾችና ለተጨማሪ 7 የቡድኑ አሰልጣኞች ቡድንና አመራሮች በአጠቃላይ 42 አባላት ሜዳሊያ እንዲሰጥ ተወስኗል።