በአራተኛው ሳምንት የመጨረሻ ጨዋታ ኢትዮጵያ መድኅን ወላይታ ድቻን 1 ለ 0 ረቷል ።
ወላይታ ድቻዎች በሶስተኛው ሳምንት ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ነጥብ በተጋሩበት ጨዋታ ላይ ከነበረው የመጀመሪያ አሰላለፍ አንድ ለውጥ በማድረግ በአንተነህ ጉግሳ ምትክ ደጉ ደበበን ተክተዋል ። በኢትዮጵያ መድኅን በኩል ደግሞ በሳምንቱ ለገጣፎ ለገዳዲን በረቱበት ጨዋታ ላይ በነበረው ምርጥ አስራአንድ ላይ ምንም ለውጥ ሳያደርጉ ጨዋታውን ጀምረዋል ።
በጨዋታው የመጀመሪያ አጋማሽ ኢትዮጵያ መድኅኖች በኳስ ቁጥጥሩ የበላይነት በመውሰድ መጫወት የቻሉ ሲሆን ወደ ተጋጣሚ የግብ ክልል ደርሰው ጠንካራ የግብ ዕድሎቸን ከመፍጠሩ አንፃር ግን ክፍተቶች ነበሩባቸው ። በወላይታ ድቻ በኩል በተወሰደባቸው የጨዋታ ብልጫ ወደ ኋላ አፈግፍገው ለመጫወት የተገደዱ ሲሆን በተወሰኑ አጋጣሚዎች ለአጥቂው ስንታየሁ መንግስቱ በሚላኩ ኳሶች ዕድሎችን ለመፍጠር ሞክረዋል ።
- ማሰታውቂያ -
በጨዋታው የመጀመሪያ የግብ ሙከራ በ19ኛው ደቂቃ ላይ የተደረገ ሲሆን ቃልኪዳን ዘላለም ከማዕዘን ምት ያሻገረውን ኳስ ስንታየሁ መንግሥቱ በግንባር ገጭቶ ግብ ጠባቂው መልሶታል ።
ከሰባት ደቂቃዎች በኋላ ደግሞ ኢትዮጵያ መድኅኖችም ጥሩ የግብ ዕድል መፍጠር የቻሉ ሲሆን ኪቲካ ጀማ ከኡመር የደረሰውን ኳስ ወደ ግብ ሞክሮ ኳሱ ኢላማውን ሳይጠብቅለት ቀርቷል ።
ኪቲካ ጀማ በ33ኛው ደቂቃ ላይም ከቅጣት ምት የተሻገረን ኳስ በግንባር ገጭቶ ግብ ለማድረግ ቢጠርም ለጥቂት የግቡን አናት ታኮ ወጥቷል ።
መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ሊጠናቀቅ አንድ ደቂቃ ሲቀረው የወላይታ ድቻው ግብ ጠባቂ ቢንያም ገነቱ በብሩክ ሙሉጌታ ላይ በሰራው ጥፋት የፍፁም ቅጣት ምት የተሰጠ ቢሆንም የቀድሞው የሲዳማ ቡና ተጫዋች ብሩክ ሙሉጌታ የመታው ኳስ በቢንያም ገነቱ ተመልሷል ።
የመጀመሪያው አጋማሽም ያለግብ ተጠናቋል ።
በሁለተኛው አጋማሽ የተሻለ ብልጫቸውን አስቀጥለው የገቡት ኢትዮጵያ መድኅኖች ጫን ብለው በመጫወት ኳስ እና መረብን ለማገናኘት የሚያደርጉትን ጥረቶች አጠናክረው ቀጥለዋል ።
አጋማሹ ለደቂቃዎች ጠንከር ያለ የግብ ዕድል ሳያሳየን ቢቆይም በ67ኛው ደቂቃ ላይ ፒተር ሳይመን ከአብዱልከሪም መሀመድ የተሻገረለትን ኳስ በግንባር ገጭቶ የግቡ አግዳሚ መልሶበታል ።
ከአራት ደቂቃዎች በኋላ ኢትዮጵያ መድኅኖች የወላይታ ድቻን የኳስ ቅብብል በማቋረጥ በፈጣን ወደ ተጋጣሚ የግብ ክልል ያደረሱትን ኳስ ብሩክ ሙሉጌታ አሻግሮ በኡመር በኩክ ለፒተር የደረሰውን ኳስ አጥቂው ከመረብ አሳርፎታል ።
ከግቡ በኋላ ከጨዋታው ቢያንስ አንድ ነጥብ ለማግኘት ጥረቶችን ያደረጉተሰ የጦና ንቦቹ በ83ኛው ደቂቃ ላይ ዮናታን ኤሊያስ ከሳጥኑ የቅርብ ርቀት ከቅጣት ምት ወደ ግብ የላከውን ኳስ አቡበከር ኑሪ በድንቅ ብቃት ግብ ከመሆን አድኖታል ።
በመጨረሻም ኢትዮጵያ መድኅን በ1 ለ 0 ውጤት አሸንፏል ።
በአምስተኛው ሳምንት ጨዋታዎች በመጪው ጥቅምት 16(ረቡዕ) 10:00 ላይ ኢትዮጵያ መድኅን ከመቻል ሲጫወት በተከታዩ ቀን 7:00 ላይ ወላይታ ድቻ ሀድያ ሆሳዕናን ይገጥማል ።