የኢትዮጵያ ብሄራዊ የዳኞችና ኮሚቴ የዳኝነት ስህተት ፈጽመዋል ውጤትም ለውጠዋል ያላቸው ዳኞች ላይ የቅጣት ውሳኔ አሳልፏል።
በኮሚቴው ውሳኔ መሠረት ድሬዳዋ ከተማ ከሀድያ ሆሳዕና ጋር በተደረገ ጨዋታ ሶስት የተሳሳተ የፍጹም ቅጣት ምት የሰጠው ፌዴራል አርቢትር አለማነሁ ለገሠን ለ6 ወራት ከዳኝነት አግዷል። አዲስ አበባ ከተማ ከመከላከያ ባደረጉት ጨዋታ ላይ የተሳሳተ ውሳኔ ወስኗል የተባለው ፌዴራል አርቢትር ብርሃኑ መኩሪያና አዳማ ከሀድያ ሆሳዕና ጋር ሲጫወቱ የሀድያ ሆሳዕና ግብ ጠባቂ ከፍጹም ቅጣት ክልል ውጪ ወጥቶ ኳስ በእጁ በመንካቱ ቀይ ካርድ ማሳየት ሲኖርበት የቢጫ ካርድ መዟል የተባለው ፌዴራል አርቢትር ምስጋናው መላኩ 6 ወር እንዲታገዱና ከፍተኛ ሊግ ወርደው እንዲያጫውቱ ተወስኗል።
ከዚህም በተጨማሪ ቅዱስ ጊዮርጊስና ጅማ አባጅፋር ሲጫወቱ የተሳሳተ ውሳኔ አሳልፏል የተባለው ረዳት ዳኛው መሀመድ ሁሴንን በማስጠንቀቂያ አልፎታል። የዚህ ጨዋታ የመሃል ዳኛ ኢንተ.አርቢትር ሊዲያ ታፈሰና መከላከያ ከኢት.ቡና ሲጫወቱ ተገቢ ያልሆነ የፍጹም ቅጣት ምት የሰጠው ኢንተ.አርቢትር ቴዎድሮስ ምትኩን በጽሁፍ ማስጠንቀቂያ አልፏቸዋል።
የኮሚቴው የቅጣት በትር ኮሚሽነሮችንም የነካ ሲሆን ለሊግ ኩባንያውና ለዳኞች ኮሚቴ አወዛጋቢ የሆነ የተለያየ ሪፖርት አቅርበዋል ያላቸውን ኮሚሽነር መኮንን አስረስን ለስድስት ወር አግዷል። ከዚህም ውጪ ኮሚሽነር ሰላሙ በቀለና ኮሚሽነር ሰርካለም ከበደን በከባድ ማስጠንቀቂያ አልፏቸዋል።