….3 ክለቦች ለዋንጫ
…11 ክለቦች ላለመውረድ ተፋጠዋል….
“ቅዱስ ጊዮርጊስን አሸንፈን ድሉን ለተጎዱት ደጋፊዎቻችን
መታሰቢያ እናደርገዋለን”
አሰልጣኝ ደግአረገ ይግዛው
/ ባህርዳር ከተማ/
“ከባህርዳር ከተማ የሚገጥመንን ትግል በድል ለመወጣትና ልዩነቱን ለማስፋት ተዘጋጅተናል”
አሰልጣኝ ዘሪሁን ሸንገታ
/ቅዱስ ጊዮርጊስ/
የአምስት ጨዋታ መርሃግብር ብቻ በቀረው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ወራጅ ላለመሆን የሚፋለሙት ክለቦች 11 መሆናቸው አነጋጋሪ ሆኗል።
- ማሰታውቂያ -
እስካሁን በተካሄደው የ25 ሳምንት መርሃግብር 15ኛ እና 16ኛ ደረጃ ላይ ያሉት ኢትዮ ኤሌክትሪክና ለገጣፎ ለገዳዲ መውረዳቸውን ተከትሎ 4ኛ ደረጃ ላይ ካለው ፋሲል ከነማ ጀምሮ እስከ 14ኛ ደረጃ ላይ ካለው አርባምንጭ ከተማ ድረስ ያሉት 11 ክለቦች ሀድያ ሆሳዕና ፣ ኢትዮጵያ ቡና ፣ ሃዋሳ ከተማ ፣ አዳማ ከተማ፣ መቻል ፣ ድሬዳዋ ከተማ ፣ ሲዳማ ቡና ፣ወላይታ ድቻና ወልቂጤ ከተማ አንደኛው ወራጅ ክለብ ላለመሆን በቀሪዎቹ ጨዋታዎች የሚያደርጓቸው ፍልሚያዎች አጓጊ ሆኗል።
በተቃራኒው በሊጉ በእስካሁኑ ውጤት 55 ፣ 50 እና 45 ነጥቦች የያዙት ቅዱስ ጊዮርጊስ ፣ ባህርዳር ከተማና ኢትዮጵያ መድን ብቻ ለዋንጫ እየተፋለሙ ሲሆን ነገ ምሸት 12 ሰዓት ላይ በ26ኛው ሳምንት መርሃግብር መሪዎቹ ቅዱስ ጊዮርጊስና ባህርዳር ከተማ የሚያደርጉት ጨዋታ ትኩረት ስቧል። ጨዋታው 55 እና 50 ነጥቦች በያዙት የአሰልጣኝ ዘሪሁን ሸንገታ ቅዱስ ጊዮርጊስና የአሰልጣኝ ደግአረገ ይግዛው ባህርዳር ከተማ መሃል የሚደረገው ፍልሚያ የነጥብ ልዩነቱ ጠብቦ በሊጉ ፉክክር ላይ ነፍስ የመዝራትና ርቀቱ ሰፍቶ ላይ ፍልሚያው ላይ ውሃ የመቸለስ አቅም ያለው መሆኑ ትልቅ ግምት ተሰጥቶታል የፌዴሬሽኑ የዳኞች ኮሚቴም ከሊጉ የውድድር ኮሚቴ ተወካይ ጋር በዳኝነቱ ምርጫ ላይ ጥንቃቄ እንደሚያደርግ ይጠበቃል።
በጨዋታው ዋዜማ ዛሬ ጠዋት በደጋፊዎቹ ላይ የደረሰው አደጋ ሙሉ ቡድኑን እንዳሳዘነ ለሀትሪክ ድረገፅ አስተያየቱን የሰጠው አሰልጣኝ ደግአረገ ይግዛው እንደገለፀው “በምንወዳቸው ደጋፊዎቻችን ላይ የደረሰው አደጋ ስሜት የሚነካ ነው እንዲህ ሊሆንም አይገባም ነበር እንደ ሀገርም ለወደፊቱ ያሰጋል ያም ሆኖ ጉዳት የገጠማቸው እህት ወንድሞቻችን ፈጣሪ እንዲፈውሳቸው እንመኛለን በርግጥም ተጨዋቾቻችን አደጋውን ሲሰሙ ስሜታቸው ተጎድቷል” ሲል ተናግሯል። “በአደጋው ስሜታቸው የተጎዳው ተጨዋቾቻችንን አረጋግተን ዛሬ ሙሉ ልምምዳችንን በስኬት አጠናቀን ለጨዋታው ዝግጁ ነን” ያለው አሰልጣኙ “ጨዋታውን እንፈልገዋለን ለተጎዱት እህት ወንድሞቻችን ማስታወሻ በሚሆን መልኩ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር ያለብንን ጨዋታ አሸንፈን ለተጎዱት ደጋፊዎቻችን መታሰቢያ እናደርገዋለን ለዚህም ያለንን አቅም አውጥተን ለማሸነፍ እንጥራለን” ሲል አስረድቷል።
አሰልጣኝ ደግአረገ “ቀሪው አምስት ጨዋታ አለ ለሁሉም ትኩረት ሰጥተን መጫወት ይጠበቅብናል ቅዱስ ጊዮርጊስን ረትተን በቀሪዎቹ ነጥብ ብንጥል ትርጉም ስለሌለው ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጨዋታ ጀምሮ ለሁሉም ትኩረት ሰጥተን እንጫወታለን ነገር ግን ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር የምናደርገው ጨዋታ ጠንካራ ወደ ፊት የምናደርገውን ጉዞ የሚወስን በመሆኑ ትኩረት የምንሰጠው ይሆናል ለእኛም ሶስት ነጥብ ከጨዋታው መውሰድ ርቀታችንን የምናጠብበት የጊዮርጊስን ጉዞ የምንገታበት የሊጉን የፉክክር መንፈስ የምንጠብቅበት በመሆኑ ለማሸነፍ እንጥራለን” ሲል ተናግሯል።
ቡድኑን ከአምስት አመት በኋላ ለሊግ ሻምፒዮንነት የመራው የፈረሰኞቹ አሰልጣኝ ዘሪሁን ሸንገታ በበኩሉ እንደገለፀው ” በጥሩ ሁኔታ ዝግጅት አድርገናል ጠንካራ ልምምድ ሰርተን ለነገው ጨዋታ ተዘጋጅተናል ጉዳት ላይ የነበረው አማኑኤል ገ/ሚካኤልም ከጉዳቱ አገግሞ በግሉ ልምምድ እየሰራ ነው ከሱ ውጪ ሌሎቹ ሙሉ የቡድናችን አባላት ለፍልሚያው ዝግጁ ናቸው ከባህርዳር ከተማ ጠንካራ ትግል እንደሚጠብቀን እናውቃለን ያም ቢሆን አሸንፈን ጉዟችንን ለማሳመር ተዘጋጅተናል ” ሲል ተናግሯል።
“የሚጠበቀውን እየሰራን እግዚአብሄር እንዲባርክልን እንፀልየለን አሁን የደረስነው ቦታ የደረስነው በጠንካራ ስራ በመሆኑ ስራችንን ጠንክረን እንሰራለን እያንዳንዱን ጨዋታ ለማሸነፍ እንጥራለን የምንለየው ጨዋታ የለም ከእግዚአብሄር ጋር ውጤቱን ለማምጣት እየሰራን ነው አሁን ስለ ዋንጫው አናስብም በተከታታይ ሁለት አመት ዋንጫ ስለ መውሰድ ጊዜው ገና ነው” ያለው አሰልጣኙ “ለእኛ ከ15ቱ ክለቦች ጋር የምናደርጋቸው 30 ጨዋታዎች ሁሌ ጠንካራና ለዋንጫ እንደመጫወት ጠንካራ ፍልሚያ የሚደረግባቸው ናቸው በብዙ ነገር ተፈትነን ነው ለዚህ የደረስነው ከባህርዳር ከተማ የሚገጥመንን ትግል በድል ለመወጣትና ልዩነቱን ለማስፋት ተዘጋጅተናል” ሲል ተናግሯል።
አሰልጣኙ በባህርዳር ከተማ ደጋፊዎች ላይ ስለደረሰው ጉዳት በሰጠው አስተያየት “በወገኖቻችን ላይ በደረሰው ጉዳት አዝኛለሁ ከጉዳታቸው ቶሎ እንዲያገግሙ እመኛለሁ የሞተም ባለመኖሩ ደስ ብሎኛል እግዚአብሄር ፅናቱን እንዲሰጣቸው እመኛለሁም” ብሏል።
በሊጉ የ26ኛው ሳምንት መርሃግብር ከቅዱስ ጊዮርጊስና ባህርዳር ከተማ አስቀድሞ ከቀኑ 9 ሰአት ላይ መውረዱን ያረጋገጠው ለገጣፎ ለገዳዲ ከአዳማ ከተማ ይጫወታሉ
መርሃግብሩ ቅዳሜ ሲቀጥል መቻል ከሀዋሳ ከተማ አርባምንጭ ከተማ ከወረደው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ጋር ይጫወታሉ።
በዕለተ እሁድም ጨዋታዎቹ ሲቀጥሉ ድሬዳዋ ከተማ ከፋሲል ከነማ ሲዳማ ቡና ከወላይታ ድቻ ይጫወታሉ የ26ኛው ሳምንት መርሃግብር የመጨረሻ የጨዋታ ቀን ሰኞ ኢትዮጵያ መድን ከወልቂጤ ከተማ ሀድያ ሆሳዕና ከኢትዮጵያ ቡና ይጫወታሉ።