*…ከፌዴራል ፖሊስ ጋር በጋራ ለመስራት ተዘጋጅቷል
*….ከፌዴሬሽኑ ጋር በቀጣይ ሳምንት ይፈራረማሉ..
“ሊጉ ከስጋት ነጻ ሆኖ ውድድር ማካሄድ እንደምንችል
ዲ.ኤስ.ቲቪ ማረጋገጥ ይፈልጋል ይህን የሚያረጋግጠው ደግሞ ፌዴራል ፖሊስ ነው”
መቶ አለቃ ፈቃደ ማሞ
/የፕሪሚየር ሊጉ አክሲዮን ማህበር ፕሬዝዳንት/
” የእግርኳስ ስኪልን ከማሳደግ ይልቅ ማጭበርበሮቹ ከፍተኛ ናቸው እኔ ከመጣው ጀምሮ ማጭበርበሩ አለ ይህን ለማስተካከል ከህግ ይልቅ አስተሳሰብ ወሳኝ ነው”
አቶ ክፍሌ ሰይፈ
/ የሊጉ ዋና ስራ አስኪያጅ/
- ማሰታውቂያ -
“አንድን የጨዋታ ዳኛ ቡድኖችን ከአቅም በታች ተጫውተዋል ለማለት የሚያስችለው ህጎች የሉም ሲዳማ ላይ ያየነው የተራቀቀ መላቀቆች እያወቅን የህግ መብት ስለሌለን የተውናቸው ናቸው” ሲል የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማህበር አስታወቀ።
የፕሪሚየር ሊጉ አክሲዮን ማህበር ፕሬዝዳንት መቶ አለቃ ፈቃደ ማሞና የአክሲዮን ማህበሩ ዋና ስራ አስኪያጅ
አቶ ክፍሌ ሰይፈ ጋር በመሆን ትላንት በኤሊያና ሆቴል በሰጡት መግለጫ ከጨዋታ ማጭበርበር ጋር ተያይዞ ሸፍጦች እንዳሉ አምነዋል። ” የእግርኳስ ስኪልን ከማሳደግ ይልቅ ማጭበርበሮቹ ከፍተኛ ናቸው እኔ ከመጣው ጀምሮ ማጭበርበሩ አለ ይህን ለማስተካከል ከህግ ይልቅ አስተሳሰብ ወሳኝ ነው የሁሉንም ክለቦች አሰልጣኞች ቡድን መሪ ጠርተን የማጭበርበር ድርጊት እንዳይከሰት አሳስበን ነበር ከዳኞች መሃል ያሰለጠኑ፣ ያስተማሩ፣ ልምድ ያላቸውን በምስጢር አዋቅረን ነበር የተገኘ ለውጥ ግን አልነበረም ስህተቱ ዳኞች፣ አሰልጣኞችና ተጨዋቾች እያለ ወረደ አሁን ግን ከህጉ ጎን ፕሮፌሽናል አስተሳሰብ መያዝ አለበት” ሲል ስራ አስኪያጁ ተናግሯል።
ከደመወዝ አለመክፈል ዙሪያ ጉባኤው ጠንካራ ውይይት ማድረጉን የገለጹት መቶ አለቃ ፈቃደ ” በደመወዝ ክፍያ ደቡበ አፍሪካ፣ ግብጽና ኢትዮጵያ ከአንድ እስከ ሶስት ያለውን ደረጃ ይዘዋል በኳሱ እድገት ግን ሰማይና ምድር ናቸው ከደመወዝ ክፍያ ጋር ክለቦቻችን በአማካይ ለደመወዝ የምናውለው ከ45 ሚሊየን ብር በላይ ነው ብለዋል ይሄ ግን ልክ አይደለም ለወደፊቱ 99 በመቶ ለደመወዝ አውሎ መቀጠል የለም አደብ የሚያስገዛ ህግ እናወጣለን ለአሁኑ ግን በጉባአው በከፍተኛ ደመወዝ ተጨዋች ቀጥራችሁ ሩብ አመት ሳይሞላ ደመወዝ መክፈል ያቅታችኋል በዚህ አይነት ውድድሩ እንደሚጨረስ ምን ማስተማመኛ አለን ብለን አልጠየቅንም መክፈል ያልቻለ ክለብ ነጥብ እንቀንሳለን ብለን የምንቀጣበት ህግም ደግሞ የለም” ሲሉ የህግ ክፍተቱን ገልጸዋል።
“ክለቦቹ ኢትዮጵያ ውስጥ ለተጨዋችችና ለአሰልጣኝ ከፍተኛ ደመወዝ እየከፈሉ እግርኳሱ እየተጎዳ ነው አንድ በሉን ብለው ሲጠይቁን አድራጊው እነሱ ሆነው እንዴት ጠየቁን ብለን ተገርመናል ዘንድሮ ደቡቡ ከፍተኛ ገንዘብ ካወጣ በቀጣይ አመት ሰሜኑ ያወጣል ዝርፊያው በየተራ ይመስላል ምክንያቱ ደግሞ ዋንጫ ለማምጣት ይሉናል ዋንጫ በገንዘብ አይመጣም አሁንም ክለቦቹ ተያይዘው ወደ ገደል እየሄዱ ነው” ሲሉ ስጋቱን ይፋ አድርገዋል
ስለ ደመወዝ ክፍያ ገደብ የተጠየቁት ፕሬዝዳንቱ “የ50 ሺህ ብሩ የደመወዝ ገደብ ድጋሚ እንዲነሳ አንዳንዶቹ ክለቦች ይፈልጋሉ ከዚህ በፊት ክለቦችና ባህልና ስፖርት ሚኒስቴሩ ቁጭ ብለው ገደቡን ወሰነዋል ይሄን ለማድረግ የህግ መብት ግን የለም ካፍም ፊፋ ጋርም የለም አሁንም ግን አንዳንድ ክለቦች ፈልገው ነበር ህጉ በፍጹም ተመልሶ አይመጣም ህገወጥ ነው” ሲሉ አብራርተዋል።
“የክለብ ላይሰንሲጉንጉ ጉዳይ አስገዳጅ እየሆነ ነው
ለምሳሌ ካፍ ሁሉም የአፍሪካ ሀገራት አዲስ የውድድር ጅማሯቸውን ነሀሴ 1 እንዲጀመሩ ሊያደርግ እየሰራ ነው ከተወሰነ አለመተግበር አይቻልም በአሁኑ ጊዜ የክለብ ላይሰንሲንግ ፍተሻው ጠንካራ ቢሆን ኖሮ ቅዱስ ጊዮርጊስና ባህርዳር ከተማ አያልፉም ነበር ” በማለት ካፍ ጠንካራ አቋም እየያዘ መሆኑን መቶ አለቃ ገልጸዋል። የአክሲዮን ማህበሩ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ክፍሌ ሰይፈም ይህን የመቶአለቃ ሃሳብ ያጠናከረ ሲሆን “ሊጉ የቆየ ሊግ ነው በክለብ ላይሰንሲንግ ስታንዳርድ ግን ኋላቀር ነው ክለቦችን አግዘን ህጉን እንዲያሟሉ እንሰራለን ይሄ የግድ ነው ” ሲል ተናግሯሬል።
ከጸጥታ ጋር ተያይዞ አስተያየታቸውን የሰጡት መቶ አለቃ ፈቃደ ” የግል የጸጥታ ሃይሎች ለኛ አስተማማኝ አይደሉም … የሀገሪቱን ደህንነት የሚያስጠብቀው ፌዴራል ፖሊስ በመሆኑ ከነሱ ጋር ተፈራርመን ወደ ስራ መግባትን መርጠናል ሊጉ ከስጋት ነጻ ሆኖ ውድድር ማካሄድ እንደምንችል ዲ.ኤስ.ቲቪ ማረጋገጥ ይፈልጋል ይህን የሚያረጋግጠው ደግሞ ፌዴራል ፖሊስ ነው በቀጣይ መጠጥ ጠጥቶ የገባን 500 ብር ቢቀጣ የተጣላ ደግሞ ሳምንት ትታሰራለህ የሚለው መጠነኛ
ፍ/ቤት ሊቋቋም የሚችለው ሁሉ በፌዴራል ፖሊስ ነው” ሲሉ አስረድተዋል።
ከፌዴሬሽኑ ጋር ስላላቸው የስራ ግንኙነት ያብራሩት መቶ አለቃ የጎላ ልዩነት የተከሰተው በለገጣፎ ለገዳዲ ፎርፌ ዙሪያ ላይ መሆኑን አምነው አሁን ላይ ግን መግባባት ላይ መደረሱን አስረድተዋል… “ከፌዴሬሽኑ ጋር የየድርሻችን ሃላፊነት ወስደናል የሚያገናኘንና የሚለየንን ለይተን ተወያይተን ተስማምተናል..በቀጣዩ ሳምንት እንፈራረማለን” ሲሉ ገልጸዋል።
ስለ ሜዳዎች የተጠየቁት ፕሬዝዳንቱ ” ፕሪሚየር ሊጉ ሲጀመር አዲስ አበባ፣አዳማ፣ ባህር ዳር፣መቀሌ፣ ድሬዳዋና አዋሳ ነበሩ ….ዛሬ ግን መቀሌ፣ አዲስ አበባ፣ ባህር ዳርና ሀዋሳ የሉም ምናልባት አዲስ አበባ ይመለስ ይሆናል… አዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታ ቢካሄድበትኮ ወላይታ ድቻ ፣ወልቂጤ ከተማና ሀድያ ሆሳዕና ከፍተኛ ገቢ ያገኛሉ እንደ ሊግ ዛሬ በአዲስ አበባ ሲጀመር ደስ ይለናል እንደ ሀገር ግን ካፍ ካላረጋገጠው ብሄራዊ ቡድኑ መጫወት አይቻልም” ሲሉ የሜዳውን ችግርና ያለውን ሂደት አብራርተዋል።
ሁለቱም አመራሮች በጋራ በሰጡት መግለጫ በወጣው መርሃግብር መሰረት ፕሪሚየር ሊጉ እሁድ መስከረም 20/2016 አዳማ ከተማ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሲዳማ ቡና ከኢትዮጵያ ቡና በሚያደርጓቸው ሁለት ጨዋታዎች እንደሚጀመር አረጋግጠዋል።