በአሰልጣኝ ዮርዳኖስ አባይ እየተመራ በዘንድሮዉ የውድድር አመት መጀመሪያ ላይ በርከት ያሉ ጨዋታዎቹን በአቻ ዉጤት ሲያጠናቅቅ የነበረዉ ድሬዳዋ ከተማ ከሰባተኛዉ የጨዋታ ሳምንት አንስቶ በሜዳዉ ያደረጋቸዉን ሶስት ጨዋታዎች በድልመወጣቱ የሚታወስ ሲሆን በዛሬዉ ዕለት ደግሞ የሊጉን መሪ ኢትዮጵያ መድድን በቻርለስ ሙሴጌ ሁለት እና እና አሳንቴ ጎድፍሬድ ጎሎች ታግዞ ሶስት ለአንድ በሆነ ዉጤት መርታት ችሏል።
በሊጉ እስከ ስምንተኛዉ ሳምንት ድረስ በቅዱስ ጊዮርጊስ እና ባህርዳር ከተማ ብቻ ተሸንፎ የነበረዉ እና በቀሪ ጨዋታዎች ሁሉንም በድል በመወጣት በአስራ ስምንት ነጥብ ሊጉን በመምራት ላይ ይገኝ የነበረዉ ኢትዮጵያ መድን በዛሬው ዕለት በዘጠነኛው ሳምንት በድሬዳዋ ከተማ ሶስት ለአንድ በሆነ ዉጤት ሲሸነፍም የማስተዛዘኛዋን ብቸኛ ግብ የመስመር ተጫዋቹ ሀቢብ ከማል ማስቆጠር ችሏል።
ወጤቱን ተከትሎም ባለፉት ስድስት ጨዋታዎች አንድም ሽንፈት ያልገጠመዉ እና መቻል ፣ ኢትዮጵያ ቡና እና ኢትዮጵያ መድንን የመሳሰሉ ትልልቅ ክለቦችን ማሸነፍ የቻለዉ የዮርዳኖስ አባዩ ድሬዳዋ ከተማ በአስራ አራት ነጥብ በጊዜያዊነት አምስተኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ ፤ በተቃራኒው በዛሬዉ ጨዋታ ሽንፈት ያስተናገደዉ የገ/መድህን ሀይሌዉ ኢትዮጵያ መድን በአስራ ስምንት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ችሏል።
በቀጣይ በአስረኛዉ ሳምንት የሊጉ መርሐግብርም በዚህኛዉ የጨዋታ ሳምንት ሽንፈትን ያስተናገዱት ኢትዮጵያ መድን ከሀዋሳ ከተማ ጋር ሲገናኙ በተቃራዉ ባለሜዳዉ ድሬዳዋ ከተማ ከወልቂጤ ከተማ የሚጫወቱም ይሆናል።