በህንድ አስተናጋጅነት በ 2022 ለሚካሄደው የፊፋ ከ 17 ዓመት በታች የሴቶች የዓለም ዋንጫ ለማለፍ የቅድመ ማጣሪያ የእጣ ማውጣት መርሃ ግብር ዛሬ ከሰዓት በኋላ በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) ዋና መሥሪያ ቤት በግብፅ ካይሮ ተካሂዷል ፡፡
የካፍ ውድድሮች ዳይሬክተር ካሌድ ናሳር በግብፅ የሴቶች ብሄራዊ ቡድን እግር ኳስ ተጫዋች ናዲን ጋዚ ጋር በጋራ በመሆን የዕጣ ማውጣት ስነ-ስርዓቱ ተካሂዷል ፡፡
በመጀመሪያው ዙር የማጣርያ ጨዋታ ሩዋንዳ ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ፣ኤርትራ ከ ደቡብ ሱዳንን እንዲሁም ኬንያ ከ ኢኳቶሪያል ጊኒ ጋር ጨዋታቸውን የሚያካሂዱ ይሆናል ፡፡
በአስር ሀገራት መካከል የሚደረገው የመጀመሪያው ዙር የማጣርያ ጨዋታ ከጥር 5 እስከ 21/2014 ባለው ጊዜ ውስጥ ይደረጋል ፡፡
- ማሰታውቂያ -
በሁለተኛው ዙር ማጣርያ ጨዋታቸውን የሚጀምሩት የኢትዮጵያ ሴቶች ከ 17 ዓመት ብሔራዊ ቡድን ከ ዩጋንዳ አቻቸው ጋር ጨዋታቸውን የሚያካሂዱ ይሆናል፡፡
ኢትዮጵያ ከ ዩጋንዳ ጋር በምታካሄደው የሁለተኛ ዙር ጨዋታ ድል የሚቀናቸው ከሆነ በ ሶስተኛው ዙር ( የ ኬንያ / ኢኳቶሪያል ጊኒ ) አሸናፊ ከ ደቡብ አፍሪካ ጋር ተጫውቶ የሚያልፈው ሀገር ጋር የመጫወት እድል አላቸው ።
በህንድ አለም ዋንጫው አፍሪካ በሶስት ሀገራት ስትወከል በአጠቃላይ ሀያ ዘጠኝ ሀገራት በማጣሪያው ተካተዋል ፡፡
ለአለም ዋንጫው ለማለፍ ሀገራት አራት ዙሮችን በማጣርያ እንደሚጫወቱ በወጣው መርሐ ግብር ለማወቅ ተችሏል ።
በተያያዘ ዜና ለ 2022 የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ሉሲዎቹ በመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ በተመሳሳይ ከ ዩጋንዳ አቻቸው ጋር የመጀመሪያ ጨዋታቸውን የሚያካሄዱ ይሆናል ።
ሉሲዎቹ የመጀመሪያ የደርሶ መልስ የማጣርያ ጨዋታቸውን ከ ግንቦት 30 እስከ ሰኔ 8 ባሉት ቀናት እንደሚያደርጉ የወጣው መርሐ ግብር ያሳያል ።