የ2013 የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ዋንጫ አሸናፊው ፋሲል ከነማ ኢትዮጵያን በአፍሪካ ቻምፒየንስ ሊግ ውድድር የሚወክል ሲሆን ለቅድመ ማጣሪያ ጨዋታ እና ለ2014 ዓመት የሊጉ ፍልሚያ ተጠናክረዉ ለመቅረብ የነባር ተጫዋቾችን ውል በማደስ አዲስ ወሳኝ ተጫዋቾችን በማስፈረም መደበኛ የቅድመ ዉድድር ዝግጅታቸውን በውቢቷ ባህርዳር ከተማ በማድረግ ላይ የሚገኙት ፋሲል ከነማዎች በዛሬዉ ዕለት መስከረም 2/2014 ዓ.ም ከቀኑ 10:00 ላይ በባህርዳር አለምአቀፍ ስታዲየም የአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ የመጀመሪያ ማጣሪያ ጨዋታቸዉን የሚያደርጉ ይሆናል።
አፄዎቹ ከአሰልጣኝ ስዩም ከበደ ጋር ለመቀጠል ውላቸውን ካደሱ በኋላ ዳግመኛ የሊጉ ሻምፒዮን ለመሆን እንዲሁም በአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ ማጣሪያ በማለፍ በውድድሩ ተሳትፏቸውን ለማድረግ አስቀድመው ለተጫዋቾች ጥሪ በማድረግ ማረፊያቸውን አዲስ አምባ ሆቴል አድርገው በባህርዳር አለማቀፍ ስታዲየም የመለማመጃ ሜዳ እና በጅምናዚየም በቀን ሁለት ጊዜ በአካል ብቃት ላይ ትኩረት አድርገው ልምምዳቸውን በመስራት ወራት ያስቆጠሩ ሲሆን የጨዋታው ቀን መቃረቡን ተከትሎ በቀን ሁለት የነበረውን ልምምድ አንድ ጊዜ በማድረግ ዝግጅታቸውን በተገቢው መንገድ ማጠናቀቃቸው ታዉቋል።
በአፄዎቹ ስብስብ ውስጥ ለብሔራዊ ቡድን ግልጋሎት ጥሪ የተደረገላቸው አምበሉ ያሬድ ባየህ ፣ ሽመክት ጉግሳ ፣ ሱራፌል ዳኛቸው ፣ ሀብታሙ ተከስተ ፣ ይሁን እንደሻው ፣ በዛብህ መለዩ እና አዲስ ክለቡን የተቀላቀለው አስቻለው ታመነ በብሔራዊ ቡድን ለአለም ዋንጫ ማጣሪያ የቅድመ ዝግጅት ስልጠናቸውን በዋሊያዎቹ ስብስብ ውስጥ ሲያደርጉ መቆየታቸው የሚታወስ ሲሆን ወደ ቡድናቸው ተቀላቅለው የቅንጅት ስራ በሚጫዎቱበት የባህርዳር አለማቀፍ ስታዲየም ልምምዳቸውን መከወን ችለዋል።
በተጨማሪም አፄዎቹ በታሪካቸው ለመጀመሪያ ጊዜ ተሳታፊ በሚሆኑበት የአፍሪካ ቻምፒዮንስ ሊግ የቅድመ ማጣሪያ ጨዋታ ደጋፊዎች ሜዳ ተገኝተው ቡድናቸውን እንዲያበረታቱ ለማድረግ በክለቡ አመራሮች በኩል ከፍተኛ ጥረት ቢደረግም የኮቪድ በሽታ ወረርሽን ሁኔታን ግምት ውስጥ ያስገባው ውድድሩን በበላይነት የሚመራው CAF ፈቃደኛ አለመሆኑን ተከትሎ ጨዋታው ያለደጋፊ በዝግ የሚካሄድ ይሆናል።