ፊፋ ሰበታ ከተማን አስጠነቀቀ
*.. የሀድያ ሆሳዕና ይግባኝም ውድቅ ሆኗል…
ሰበታ ከተማ ለቀድሞ ግብ ጠባቂ ዳንኤል አጄ ደመወዙን የማይከፍል ከሆን በሶስት የዝውውር መስኮት ላይ እንደሚታገድ ፊፋ አስጠነቀቀ።
አለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር ለሰበታ ከተማና በግልባጭ ለፌዴሬሽኑ በላከው ደብዳቤ የግብ ጠባቂውን ቀሪ ከ600 ሺህ ብር በላይ የሆነውን ደመወዝ እንዲከፍል ይህን ውሳኔ ኢሜይሉ ከደረሳቸው ቀን ጀምሮ በ45 ቀናት ውስጥ ተፈጻሚ እንዲያደርጉ ውሳኔው የማይፈጸም ከሆነ ግን ክለቡን እንደሚያግድ አስጠንቅቋል።
ክለቡ የፊፋን ህግ ተግባራዊ ካላደረገ እንደ ሀገርም እገዳ ስለሚኖር ሰበታ ከተማ ውሳኔውን ተፈጻሚ እንዲያደርግ ክትትል የማድረግ ሀላፊነት እንዳለበት ተገልጿል። ከ45 ቀናት በኋላ ፊፋ የዝውውር ሲስተሙን ስለሚዘጋው እንደ ሃገር ውስጥ ተጨዋቾች ጉዳይ ፌዴሬሽኑን የማግባባት ስራ መስራት እንደማይቻል ታውቋል። ግብ ጠባቂው ዳንኤል አጄ የሊጉን ክለቦች ሲከስ ለሁለተኛ ጊዜ ሲሆን ጅማ አባጅፋርን ከስሶ በፊፋ አስገዳጅነት ደመወዙን ማግኘቱ ይታወሳል።
- ማሰታውቂያ -
በጉዳዩ ዙርያ ከሀትሪክ ጥያቄ የቀረበላቸው የሰበታ ከተማ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ አለማየሁ ምንዳ በበኩላቸው “መከሰሳችንን ሳናውቅ የፊፋ ውሳኔ ደርሶናል ክሱን አለማወቃችን ቅር አሰኝቶናል ያም ሆኖ ተጨዋቹ ያቀረበውን ክስና የፊፋን ውሳኔ አልተቀበልነውም በኮቪድ ወረርሽኝ ጊዜ ኳሱ ተቋርጧል ተጨዋቹም የከሰሰው በኮቪዱ ጊዜ ተቋርጦም ቢሆን ደመወዜ ሊከፈለኝ ይገባል ብሎ ነው የሀገራችን ተጨዋቾች በወቅቱ ችግሩን ተረድተው ደመወዝ ክፈሉን አላሉም ዳንኤል አጄስ ከሌሎቹ በምን ተለይቶ ነው ክፈሉኝ የሚለው?እኛም የፊፋን ውሳኔ ተቃውመን ምላሽ የምንሰጥ ይሆናል” ሲሉ ተናግረዋል።
በሌላ በኩል በኢትዮዽያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የዲሲፕሊን ኮሚቴ የተላለፈውን ውሳኔ በመቃወም ይግባኝ የጠየቀው ሃድያ ሆሳዕና ይግባኙ ውድቅ ተደርጎበታል።
ሃትሪክ ከታማኝ ምንጭ ባገኘችው መረጃ ክለቡ 15 ተጨዋቾች ላይ የወሰነውን የእገዳ ውሳኔ ዲሲፕሊን ኮሚቴ ውድቅ በማድረግ የተጨዋቾቹ ያልተከፈለ ቀሪ ደመወዛቸውን እንዲከፍል ጥቅማ ጥቅሞችን አስቦ እንዲሰጥ ይህ የማይሆን ከሆነ ከፌዴሬሽኑ ጽ/ቤት ምንም አይነት ግልጋሎት እንዳያገኝ ወስኖበታል። ይህን ውሳኔ በመቃወም ሀድያ ሆሳዕናዎች ይግባኝ ቢሉም ይግባኝ ሰሚ ኮሚቴው ውድቅ በማድረግ የዲሲፕሊን ኮሚቴ ውሳኔ እንዲተገበር ትዕዛዝ ሰጥቷል።