በጥቂት ጊዜ ዉስጥ በሃገራችን እግርኳስ እና ስፖርት ላይ በመስራት እዉቅናን እና ተቀባይነት ያገኘው ጎፈሬ የስፖርት ትጥቅ አምራች ድርጅት በዛሬው ዕለትም የድርጅቱን እርከን አንድ እርምጃ ከፍ ያደረገ የስፖንሰርሺፕ ስምምነት ከደቡብ ሱዳኑ ክለብ ማላኪያ ጋር ፈፅሟል።
ለሶስት ዓመታት በሚቆየዉ በዚህ ስምምነት ላይ ከተነሱት ነጥቦች መካከልም :-
ጎፈሬ በየዓመቱ ለክለቡ የሚያስፈልጉትን ትጥቆች በሙሉ የሚያቀርብ ሲሆን ከዚህ በተጨማሪም ለደጋፊዎች በየዓመቱ አስር ሺ ማልያ በክፍያ የሚያቀርብ ይሆናል።
ስምምነቱን አስመልክቶም በስፍራው ከነበሩ ጋዜጠኞች መካከል ለቀረበላቸዉ ጥያቄ ምላሽ የሰጡት የድርጅቱ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ሳሙኤል “የዛሬው ስምምነት ድርጅታቸውን ጎፈሬን ብቻ ሳይሆን ሀገሪቷንም ወደ ፊት አንድ እርምጃ ያሻገረ ነዉ ብለዉ እንደሚያምኑ የገለፁ ሲሆን በዚህም ደስተኞች መሆናቸዉን ተናግረዋል።
- ማሰታውቂያ -
ከዚህ በተጨማሪም ጎፈሬ በሀገር ዉስጥ ክለቦች ላይ እየሰራ የሚገኘዉን ስራ በድርጅቱ ዕይታ ዉጤታማ ነዉ ወይ ተብሎ ለተነሳው ጥያቄም አቶ ሳሙኤል ”ያን ያህል ዉጤታማ ሁነናል ብለን አናምንም ምክንያቱም የኛ ዉጤታማነት የሚታየዉ በሚቀጥሉት ሁለት እና ሶስት አመታት ነዉ። ነገር ግን በአሁኑ ሰዓት ያን ያህል ባይሆንም መካከለኛ ነዉ ብለን ማለት እንችላለን” ብለዋል።
በሌላ በኩል ጎፈሬ ለምን በእግርኳስ ቡድኖች ብቻ ተወሰነ ብሎ ለተነሳላቸው ጥያቄ ስራ አስኪያጁ ሲመልሱ ” በእግርኳስ ቡድኖቹ ላይ ብቻ አልተወሰንም በተለያዩ ስፖርቶች ላይ ለሚገኙ ክለቦች የተለያዩ ትጥቆችን በማቅረብ ላይ እንገኛለን” ሲሉ ገልጸዋል።
በመጨረሻም በስፍራዉ የተገኙት የማላኪያ ክለብ ሊቀመንበር ጆሴፍ ሳሙኤል በበኩላቸው ከጎፈሬ ጋር ይሄንን ስምምነት መፈራረማቸው እጅግ እንዳስደሰታቸው እና ለጎፈሬም ራሱን በደቡብ ሱዳን ዉስጥ ለማስተዋወቅ በር የከፈተ ስምምነት መሆኑን ተናግረዋል።
ሀገር በቀሉ የስፖርት ትጥቅ አምራች ድርጅት ጎፈሬ በዚህ ወቅት ለበርካታ የሀገር ዉስጥ ክለቦች መለያዎችን እና የስፖርት ትጥቆችን በተለያዩ ዲዛይኖች እና ጥራት በመስራት እያቀረበ እንደሚገኝ ይታወቃል።