በ24ኛ ሳምንት የመክፈቻ ጨዋታ ረፋድ ላይ ተደርጎ ሀድያ ሆሳዕና ኢትዮጵያ ቡናን 1ለ0 በሆነ ዉጤት አሸንፎ ደረጃዉን አሻሽሏል። በሀድያ ሆሳዕና በኩል ከዚህ ጨዋታ አስቀድሞ ደርሶባቸው ከነበረዉ ተደጋጋሚ ሽንፈት ለማገገም 4-5-1 በሆነ አሰላለፍ ወደ ሜዳ ሲገቡ በኢትዮጵያ ቡና በኩል ደግሞ በተለመደው 4-3-3 አሰላለፍ ለጨዋታው ቀርበዋል።
በፌደራል ዋና ዳኛ ሚካኤል ጣዕመ ፊሸካ በተጀመረው የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ይዘዉት ከገቡት አሰላለፍ ጋር አብሮ የሚሄድ የጨዋታ መንገድን አስመልክተዉናል። በተለይ ኢትዮጵያ ቡና የኳስ ቁጥጥር የበላይነትን በመያዝ በሜዳዉ የመሀል ክፍል ላይ ብልጫ ቢዎስዱም በተለይ ከዕረፍት በፊት ቡናማዎቹ ይህ ነዉ የሚባል ጠንካራ የግብ ሙከራ ማድረግ ሳይችሉ ቀርተዋል።
ሀድያዎች በበኩላቸው ክፍተቶችን በመዝጋት በይበልጥ ተጠቅጥቀዉ በመከላከል ላይ ጊዜያቸዉን ሲያሳልፉ በመሀል በመሀል ደግሞ ከቡናማዎቹ ከሚገኙ ኳሶች በመነሳት በመልሶ ማጥቃት ግብ ለማስቆጠር ጥረት ሲያደርጉ ተስተዉሏል። በዚህ ሂደት በቀጠለዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ በ ደቂቃ ላይ ግብ አስመልክቶናል።
- ማሰታውቂያ -
የሀድያዉ የፊት መስመር አጥቂ ሜኬል ጆርጅ ከሜዳዉ የመሀል ክፍል በረጅሙ የተሻገረለትን ኳስ በደረቱ አብርዶ ወደ ግብ ሲልካት ከፊቱ የነበረዉ አበበ ጥላሁን በዕጁ በመንካቱ ምክንያት የተገኘዉን ፍፁም ቅጣት ምት ሳምሶን ጥላሁን ወደ ግብነት ቀይሮ ሀድያዎችን 1ለ0 እየመሩ ወደ እረፍት እንዲያመሩ ማድረግ ችሏል።
ከዕረፍት መልስ በተለይ የመጀመሪያዎቹን 15 ደቂቃዎች ይበልጥኑ ጨዋታዉን ተቆጣጥረው ግብ አስቆጥረዉ ወደ ጨዋታዉ ለመመለስ ጥረት ማድረግ የጀመሩት ኢትዮጵያ ቡናዎች አሁንም በድጋሚ የሀድያዎችን የተከላካይ ክፍል አልፈዉ የተሻለ ነገር ማድረግ አልቻሉም ነበር።
በተቃራኒው በ61ኛዉ ደቂቃ ላይ ሀብታሙ ታደሰ ግብ ጠባቂዉ በረከት ደስታ ኳሷን ለማዉጣት በሚሞክርበት ወቅት ተደርቦ ኳሷን ወደ ግብነት ቀይሯት የነበረ ቢሆንም ሀብታሙ ኳሷን በዕጅ በመንካቱ ምክንያት ግቧ ሳትፀድቅ ቀርታለች። ከዚህ ሁነት በኋላ በተደጋጋሚ የኢትዮጵያ ቡናን የግብ ክልል ሲፈትሹ የነበሩት ሀድያዎች በአማካዩቹ ሳምሶን ጥላሁን እና ተስፋዬ አለባቸዉ ጥሩ ሊባሉ የሚችሉ የግብ ሙከራዎችን ሲያደርጉ ተስተውሏል።
ከሁለተኛው አጋማሽ የዉሀ ዕረፍት በኋላ ሁለቱም ቡድኖች የተጫዋቾች ቅያሪ በማድረግ የበላይነት ለመዉሰድ ሲሞክሩ ተስተውሏል። በተለይ ተቀይሮ የገባው ሮቤል ተ/ሚካኤል 79ኛዉ ደቂቃ ላይ ለአስራት ቱንጆ ያቀበለዉን ኳስ አስራት ወደ ግብ ሲሞክራት ግብ ጠባቂዉ መሳይ ሲመልሳት የቸገኘችዉን ኳስ አቡበከር ወደ ግብ ቢቀይራት ከጨዋታ ዉጭ በሚል ሳትፀድቅ ቀርታለች። ከዚህ በተጨማሪም በ88ኛዉ ደቂቃ ላይ አበቡከር ሳጥን ዉስጥ ለአማኑኤል ያሸገረለትን ኳስ አማኑኤል ለአስራት አመቻችቶ የሰጠዉ ቢሆን አስራት ቱንጆ ዕድሉን ሳይጠቀምበት ቀርቶ ጨዋታው በዚሁ ተጠናቋል።
በቀጣይ በ25ኛ ሳምንት ጨዋታ ኢትዮጵያ ቡና ከሀዋሳ ከተማ እንዲሁም ሀድያ ሆሳዕና ደግሞ ከወልቂጤ ከተማ ጋር የሚገናኙ ይሆናል።