አስደናቂ የመጨረሻ ደቂቃ ተዓምር በታየበት የስምንተኛዉ ሳምንት የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ቀን የመጀመሪያ ጨዋታ ሀድያ ሆሳዕና እና ሀዋሳ ከተማ ጨዋታቸውን በአቻ ዉጤት አጠናቀዋል።
በተመጣጣኝ የጨዋታ እንቅስቃሴ በጀመረው የሁለቱ ክለቦች ጨዋታም ገና በ1ኛዉ ደቂቃ ላይ ሀድያ ሆሳዕናዎች ፍፁም ቅጣት ምት ማግኘት ችለዋል። በዚህም የሀዋሳዉ ተከላካይ ሰዒድ ሀሰን ብርሀኑ በቀለ ላይ ጥፋት መስራቱን ተከትሎ የተገኘውን ፍፁም ቅጣት ምት ሄኖክ አርፌጮ ቢመታም ግብ ጠባቂዉ መሐመድ ሙንታሪ አድኖበታል።
- ማሰታውቂያ -
በሜዳዉ የመሐል ክፍል የኳስ ቁጥጥር የበላይነትን ለመዉሰድ ሲጥሩ የነበሩት እና በሙከራም ረገድ የተሻሉ የነበሩት ሆሳዕናዎች በ24ኛዉ ደቂቃ ላይ መሪ ሊሆኑ የሚችሉበትን አጋጣሚ ማግኘት ችለዉ ነበር በዚህም ከቀኝ መስመር በኩል የተሻማዉን ኳስ ተከላካዩ ዳንኤል ደርቤ ለማዉጣት ሲጥር ኳሷ በተቃራኒው ወደ ራሱ የግብ ክልል አምርታ ለጥቂት በግቡ አናት ላይ ወደ ዉጭ ወጥታለች።
ከአንድ ደቂቃ በኋላ በ25ኛዉ ደቂቃ ላይ ብርሀኑ በቀለ ያሻማውን ኳስ ፀጋየ ብርሀኑ በድንቅ ብቃት ወደ ግብነት በመቀየር ነብሮቹን መሪ ማድረግ ችሏል። የመጀመሪያው አጋማሽ እስኪጠናቀቅ ድረስ ጥሩ የነበሩት እና በሙከራም ረገድ የተሻሉ የነበሩት ሀድያዎች የጨዋታዉን የበላይነት ሲቆጣጠሩ በአንፃሩ ሀዋሳ ከተማ ይህ ነዉ የሚባል ተጠቃሽ ሙከራ ማድረግ ሳይችሉ አጋማሹ ተጠናቋል።
ከዕረፍት መልስ በመጠኑም ቢሆን ሀይቆቹ ተሻሽለዉ ወደ ሜዳ መመለስ የቻሉ ሲሆን በዚህም በ50ኛዉ ደቂቃ ላይ አቻ መሆን የሚችሉበትን ዕድል አጊኝተዉ ሳይጠቀሙበት ቀርተዋል። በዚህም ከአሊ ሲለይማን የተቀበለውን ኳስ አጥቂዉ ሙጅብ ቃሲም ገፍቶ በረኛዉንም ማለፍ ቢችልም ሳይጠቀምበት ቀርቷል።
የጨዋታው ሰዓት እየገፋ በመጣ ቁጥር የአቻነት ግብ ለማግኘት ሲጥሩ የነበሩት ሀይቆቹ ይባስኑ በወሳኝ ሰዓት ግብ ተቆጥሮባቸዋል። በዚህም በ84ኛዉ ደቂቃ ላይ ከማዕዘን የተሻማዉን ኳስ ጋናዊው ተከላካይ ላዉረንስ በሚገባ ባለማራቁ ምክንያት በቅርበት ይገኝ የነበረዉ መለሰ ሚሻሞ ኳሷን ወደ ግብነት በመቀየር የነብሮቹን መሪነት ወደ 2ለ0 ከፍ ማድረግ ችሏል።
በ90+2 ደቂቃ ላይ ብርሀኑ በቀለ ኳስ በእጅ በመንካቱ ምክንያት የተገኘዉን ፍፁም ቅጣት ምት ሙጅብ ቃሲም ወደ ግብነት ቀይሮ ቡድኑን ባለቀ ሰዓት ወደ ጨወታ መመለስ ችሏል። ከአንድ ደቂቃ በኋላ በ90+3 ደግሞ በፈጣን የመልሶ ማጥቃት ሽግግር የተገኘዉን ኳስ አዲሱ አቱላ የሀድያ ተከላካዮች ስህተት ታግዞበት ለኤፍሬም አሻሞ አቀብሎት ተጫዋቹ ኳሷን ወደ ግብነት በመቀየር ጨዋታዉ 2ለ2 በሆነ አቻ ዉጤት እንዲጠናቀቅ ማድረግ ችሏል።