“ኢንተርሚዲየሪዎች መኖራቸው ለእግር ኳሱ ቢጠቅምም ካፍም ሆነ ፊፋ መኖራቸው የግድ ነው ብለው ግን አያስገድዱም”
የኢት.እግርኳስ ፌዴሬሽን
የኢትዮዽያ ፕሮፌሽናል
ተጨዋቾች ማህበር:-
“ማንኛውም ተጨዋች እስካልፈለገ
ድረስ በኤጀንት መፈረም አይገደድም”
የኢትዮዽያ ፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ማህበር ተጨዋቾች ያለ ኤጀንት እና ያለ ኢንተርሚዲየሪ ዝውውር ማድረግ አይችሉም የሚል አስገዳጅ ህግ የለም” ሲል ይፋ አደረገ።
ማህበሩ ይፋ ባደረገው ደብዳቤ “በፊፋም ሆነ በኢትዮዽያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ደንቦች መሰረት ያለ ኢንተርሚዲየሪዎች ድርድርም ሆነ ዝውውር ማድረግ አይችሉም የሚል ህግ የለም ነገር ግን ተጨዋቾች ከነሱ ጋር መስራት ከፈለጉ ደመወዝ ሲከፈላቸው
3% ብቻ ሊከፍሉ እንደሚገደዱ ማወቅ አለባቸው” ሲል አስታውቋል።
ማህበሩ ከዝውውር ጋር ተያይዞ ባስተላለፈው ባለ ስድስት ርዕስ መልዕክት ዝውውር ሲያደርጉ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ መክሮ ችግር ከተከሰተ ግን በቶሎ ለማህበሩ እንዲገልጹ አሳስቧል።
- ማሰታውቂያ -
በተመሳሳይ ዜና “የኢትዮዽያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የኢንተርሚዲየሪዎች መኖር እግር ኳሱ ላይ የሚጨምረው ነገር ቢኖርም ዝውውር ካለነሱ ግን አይደረግም የሚለው የተሳሳተ አመለካከት በመሆኑ ሃምሌ1/2013 ዝውውሩ ሲከፈት የሶስተኛ ወገን ያስፈልጋል የሚለው አስገዳጅነት የለውም በተጨዋቾቹ መልካም ፈቃድ የሚፈረም ብቻ ነው ” ሲል አስረድቷል።
“ህጉ አስገዳጅ ነው ስንል የነበረበት ጊዜ ነበር በመረጃ ልውውጥ ጊዜ በተፈጠረ ስህተት ነው ይሄ አሁን መታረም አለበት” ያለው ፌዴሬሽኑ” የአሁኖቹ ሶስተኛ ወገን ህጋዊነት ነሃሴ 30/2013 የሚጠናቀቅ በመሆኑ በተጨዋቹና ባለሙያዎቹ መሃል ትክክለኛና ተጠያቂነት ያለበት የስራ መመርያ በማስቀምጥ በተጨዋቹና ሶስተኛ ወገን መሃል ሲፈጠር የነበረውን ጸብና አለመተማመንን ለማጥፋት እንደሚሰራ አስረድቷል።
“የሶስተኛ ወገን መነሻ ተጨዋቹ ኳሱን ብቻ እንዲያስብ ሌላው አስተዳደራዊ ጉዳዮቹ ይሄው ኢንተርሚዲየሪ እንዲጨርስለት ታስቦ በመሆኑ እኛም ስንሰራበት ድጋፍ ስናደርግ ቆይተናል። ነገር ከጥቂቶቹ በስተቀር በተፈራረሙት የውል ዘመን ክፍያን ከተጨዋቾቹ ከመቀበል ውጪ ምንም ድጋፍ አላደረጉም” ያለው ፌዴሬሽኑ” ሶስተኛ ወገን ነኝ ያለው ወገን የተጨዋቾቹ አቋም ምርጥ እስኪሆን ድረስ የሚሰራ፣ ቢሮ ያለውና ስለ ስራው የሚገልጽ ዌብሳይት ያለው በአጠቃላይ ውል በሰጠው ተጨዋች የሚታምንበትና ተገቢ ክፍያ የሚጠይቅ የተጨዋቹን ህይወት በታማኝነት የሚረዳ መሆን አለበት።
ፌዴሬሸኑ እንደገለጸው “ብዙዎቹ ማህበራት ሲመሰረቱ ስራ የሚመስላቸው ፌዴሬሽኑን መቃወም ነው ይሄ ተገቢ አይደለም ውዝግቡ ተወግዶ ስለ ኳሱ ብቻ የምንወራበት በጋራ የምንሰራበት እንደሚሆን እንተማመናለን” በማለት ፌዴሬሽኑ አስታውቋል።