የቅዱስ ጊዮርጊሱ የአብስራ ተስፋዬ ስለ ዘንድሮው የቤትኪንግ ፕሪምየር ሊግ ተሳትፎአቸውና ስለራሱ ይናገራል፤ የአብስራ ምን ብሎ ይሆን? ተጨዋቹን ጋዜጠኛ መሸሻ ወልዴ አናግሮት የሰጠው ምላሽ የሚከተለውን ይመስላል፤ ተከታተሉት፡፡
ሀትሪክ፡- ከቤትኪንግ መጠናቀቅ በኋላ ጊዜህን በምን መልኩ እያሳለፍክ ነው?
የአብስራ፡- እስካሁን እረፍት ላይ ነበርኩ፤ አሁን ደግሞ ለመጪው የውድድር ዘመን በምርጥ ብቃቴ ላይ ለመቅረብ እንድችል ወደ ልምምድ ተመልሼ ቀለል ያሉ የሩጫና የጂም ስራዎችን እየሰራው እገኛለው፡፡
ሀትሪክ፡- ቤትኪንጉ ለቅ/ጊዮርጊስ እንዴት አለፈ?
- ማሰታውቂያ -
የአብስራ፡- የእዚህ ዓመት ውጤታችን ለእኛ አስደሳች አልነበረም፤ እንደ ቡድንም እንደ ግልም ጥሩ አልነበርንም፤ ከባድና ደባሪ ጊዜንም ነው ልናሳልፍ የቻልነው፤ በአጠቃላይ ቅ/ጊዮርጊስን በፍፁም የማይመጥን ውጤትንም ነው ልናስመዘግብም የቻልነው፡፡
ሀትሪክ፡- ለቅ/ጊዮርጊስ ውጤታማ አለመሆን ዋንኛው ችግርና ምክንያት የምትለው ምንድን ነው?
የአብስራ፡- የመጀመሪያው ወደ እኛ ቡድን ሁሌም ስትሄድ ትኩረትና /ፎከስ/ የሚደረገው ውጤት ላይ ስለሆነ ያን ያጣክ ጊዜ ከቡድኑ ትልቅነት አንፃር በቡድኑ ተጨዋቾች ላይ ጫናን የመቆጣጠር ችግር አለና ያን ለመመልከት ችለናል፤ ከዛ ውጪ የአሰልጣኞች መቀያየርም ሊጎዳን ችሏል፤ በአጠቃላይ በሁላችንም የቡድኑ ተጨዋቾችም ጋር ችግሮችም ነበሩና ለእዛ ውጤት ማጣታችን እኛ የቡድኑ ተጨዋቾች ተጠያቂዎችም ነን፡፡
ሀትሪክ፡- ቅ/ጊዮርጊስ ወደሚታወቅበት ውጤታማነቱ ይመለሳል?
የአብስራ፡- ይሄማ የማይቀር ነው፤ ምክንያቱም በእኛ የተጨዋችነት ዘመን ቡድኑ ውጤት እያጣ መሄዱ በጣም አስቆጭቶናል፤ አናዶናልምና ከዚህ ቡድን ጋር ዋንጫን ስታነሳ የምታገኘው ክብርና ሽልማቶችም ላቅ ያሉ ስለሆኑም የእዚህን ቡድን ክብርና ዝናን መመለስ የግድ ይለናል፤ ደግሞም ከፍተኛ ቁጭት ስላለብንም እርግጠኛ ሆኜ የምነግርህ ያን በተግባር ላይ እንደምናውለው ነው፡፡
ሀትሪክ፡- በደደቢት ምርጥ የነበረው የአብስራ በቅ/ጊዮርጊስ ምርጥ ችሎታውን ሊያስመለክተን አልቻለም?
የአብስራ፡- ይሄ የእውነት ነው፤ በደደቢት ሳለው በምርጥና በጥሩ ብቃቴ ላይ ነበር የምገኘው፤ ወደ ቅ/ጊዮርጊስ ሳመራም ከዛ በበለጠ አቋሜ እና ደረጃ ላይም በመገኘት ቡድኑን ለከፍተኛ ውጤት ለማብቃትም ነበር ወደ ቡድኑ የተጓዝኩት፤ እዚ ስመጣ ግን ከቡድኑ ውጤት ማጣት ጋር በተያያዘና ከአሰልጣኞችም መቀያየር ጋር በተገናኘ ከእኔ የጠበቅኩትን ብቃት አልተመለከትኩምና ለዛ ራሴን እወቅሰዋለሁኝ፤ በቆይታዬ እንደ ግልም ብዙ ተጠብቆብኝ ለቡድኑ ያደረግኩት ምንም ነገርም የለምና ይሄን አለማድረጌም ይቆጨኛል፤ ስለዚህም የመጪው ዘመን ላይ በሚኖረኝ የሊጉ ተሳትፎ ካለፉት የውድድር ጊዜያቶች ብዙ ነገሮችን በመማር እና ጠንክሬም በመስራት በምርጥ ብቃቴ ላይ እንደምቀርብና ቡድኔንም በስኬት እንደምጠቅመውም እርግጠኛ ነኝ፡፡
ሀትሪክ፡- የቅ/ጊዮርጊስ ተጨዋች ሆነህ ውጤት ማጣት ይለያል?
የአብስራ፡- አዎን፤ ወደ እዚህ ቡድን ስትመጣ እንደሌላው ቡድን ተቀባይነትን አታገኝም፤ የግድ ሁሌም አሸናፊነት ብቻም ነው የሚጠበቅብህ፤ ይሄ ቡድናችንን ከሌሎቹ ይለየዋልም፡፡
ሀትሪክ፡- በቤትኪንግ ፕሪምየር ሊጋችን በዲ.ኤስ.ቲቪ በመተላለፉ ምን አልክ?
የአብስራ፡- አጋጣሚው ለእኛ ስፖርተኞችም ሆነ ለስፖርት አፍቃሪው በጣም አሪፍ ነገር ነው፤ ለኳሳችን እድገትም የተሻለ ነገርን ይዞልን የሚመጣም ነው፤ አሁን ላይ ለውጦች እየታዩ ነው፤ ይሄም አስደስቶኛል፡፡
ሀትሪክ፡- ፋሲል ከነማና አቡበከር ናስር ዘንድሮ በከፍታ ማማው ላይ ተቀምጠዋል፤ በእነሱ ዙሪያ የምትለው ነገር ካለ?
የአብስራ፡- የእውነት ነው ሁለቱም አሪፍና ምርጥ የውድድር ጊዜን ነው ያሳለፉት፤ የሚገባቸውን ስኬትና ክብርንም ነው ሊጎናፀፉ የቻሉት፤ በተለይ ደግሞ ስለ አቡኪ በዚህ ዓመት ስላሳለፈው የውድድር ዘመን ምንም ነገርን መናገር አልፈልግም፤ ለእሱ የተለየ ዓመት ነው፤ ብዙ ሪከርዶችን ሊሰብርም ችሏል፤ ከዚህ በላይም ብዙ ነገርን መስራትም ይችላልና በዚሁ አጋጣሚ ለአቡኪም ለፋሲል ከነማም እንኳን ደስ ያላችሁ ልላቸው እፈልጋለውኝ፡፡
ሀትሪክ፡- ከአቡኪ ውጪ ሌለው የአንተ ምርጡ ተጨዋች ማን ነበር?
የአብስራ፡- የሐዋሳ ከተማው ወንድማገኝ ሀይሉ ተስፈኛ ተጨዋች ተብሎ ስለተሸለመ ሳይሆን እሱን እንደተመለከትኩት ጥሩ ተጨዋች ነው፤ በቤትኪንጉ ያደነቅኩትም ነው፡፡
ሀትሪክ፡- አቡኪም ወንድማገኝም በኮከብነት እና በተስፋኛ ተጨዋችነት ተሸልመዋል፤ ለነገ እኔስ አላልክም?
የአብስራ፡- እንዲህ ያሉ ስሜቶችማ ይኖራሉ፤ በቁጭትም ጠንክረህ እንድተስራም ያደርግሃልና ያን ሽልማት በቀጣይ ጊዜ ለማግኘት ጥረትን አደርጋለው፡፡