በዕለቱ ሁለተኛ ጨዋታ የተገናኙት አርባምንጭ ከተማ እና ድሬዳዋ ከተማ ምንም ግብ ሳያስቆጥሩ አንድ አንድ ነጥብ ተጋርተው ጨዋታቸውን አጠናቀዋል ።
አርባምንጭ ከተማ በ11ኛ ሳምንት ከሲዳማ ቡና አቻ በተለያዩበት ጨዋታ ከተጠቀሙት ቋሚ አሰላለፍ የሁለት ተጫዋቾች ቅያሪ በማድረግ የገቡ ሲሆን አብነት ተሾመን እና ደረጄ ፍሬውን በማሳረፍ በላይ ታደሰን እና ፀጋዬ አበራን ወደ ጨዋታው አስገብተዋል በድሬዳዋ ከተማ በኩል ደግሞ በሀዋሳ ከተማ በተሸነፉበት ጨዋታ ከነበረው ምርጥ አስራአንድ በተመሳሳይ የሁለት ተጫዋቾች ቅያሪ ያደረጉ ሲሆን አቤል ከበደን እና ብሩክ ቃልቦሬን በዳንኤል ሀይሉ እና ቢንያም ጥዑመልሳን ምትክ ወደ ጨዋታወኝ እንዲጀምሩ አድርገዋል ።
በመጀመሪያው አጋማሽ ተመጣጣኝ ሊባል የሚችል የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ የታየበት ሲሆን ወደ ግብ ክልል ደርሶ የተጋጣሚ ተከታካዮችን በመፈተን ረገድ በአንፃራዊነት አርባምንጭ ከተማዎች የተሻሉ ነበሩ ።
- ማሰታውቂያ -
የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ በግብ ሙከራዎችን አለመታገዙ ጨዋታውን ሳቢ እንዳይሆን ያደረገው ነበር ። በጨዋታው የነበረው የመጀመሪያ የግብ ዕድል በድሬዳዋ ከተማ በኩል የተደረገ ሲሆን አብዱራህማን ሙባረክ የደረሰውን ኳስ ለግቡ በቅርብ ርቀት ሆኖ የመታው ኳስ ወደ ውጪ ወቶበታል ። በአርባምንጭ ከተማ በኩል ደግሞ 15ኛ ደቂቃ ላይ ጥሩ የግብ ዕድል መፍጠር ችለው ነበር ።
አቡበከር ሻሚል ወደ ሳጥን ይዞ የገባውን ኳስ ለበላይ ገዛኸኝ ቢቀንስለትም ሄኖክ ኢሳይያስ ደርሶ ወደ ውጪ አውጥቶታል ። ሌላው በአርባምንጭ ከተማ በኩል የተደረገው ሙከራ 30ኛ ደቂቃ ላይ ሲሆን ከማዕዘን የተሻገረውን ኳስ በላይ ገዛኸኝ በጭንቅላት ገጭቶ ወደ ግብ የላከው ኳስ በፍሬው ጌታሁን ተይዟል ።
በሁለተኛው አጋማሽ በተመሳሳይ እንቅስቃሴ የቀጠለው ጨዋታ እምብዛም ከመጀመሪያው አጋማሽ የተለየ ነገር አልነበረውም ። ምንም እንኳን በአጋማሹ ጅማሮ ላይ ድሬዳዋ ከተማዎች የአጥቂ መስመራቸው ላይ ቅያሪዎችን አድርገው ቢገቡም ያን ያህል ለውጥ ያመጡ አልነበሩም ።
55ኛ ደቂቃ ላይ ራምኬል ሎክ የሚያሻማ መስሎ በቀጥታ ወደ ግብ የመታው ኳስ በግብ ጠባቂው ተመልሶ የማዕዘን ምት ሆኗል ይህንኑ የማዕዘን ምት ሲሻገር የደረሰው በርናንድ ኦቼንጌ ወደ ግብ የሞከረው ኳስ በድጋሚ በፍሬው ጌታሁን ተመልሶ በድጋሚ የማዕዘን ምት ሆኗል ።
ተቀይሮ የገባው የድሬዳዋ ከተማው አጥቂ ማማዱ ሲዲቤ ያመቻቸለትን ኳስ አብዱራህማን ሙባረክ 76ኛው ደቂቃ ላይ ወደ ግብ ቢሞክረውም በሳምሶን አሰፋ አማካኝነት ግብ ከመሆን ድኗል ።
መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ተጠናቆ በተጨማሪ ደቂቃዎች ላይ በርናንድ ኦቼንጌ ባሳየው ያልተገባ ባህሪ በሁለተኛ የቢጫ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል ።
ጨዋታውም በ0 ለ 0 ውጤት ተጠናቀቀ ።
ውጤቱን ተከትሎም አርባምንጭ ከተማ ነጥቡን 13 ሲያደርስ ድሬዳዋ ከተማ ደግሞ ነጥቡን 15 ማድርስ የቻሉ ቢሆኑም በደረጃቸው ላይ ግን ምንም አይነት ለውጥ አላደረጉም ።
በ13ኛ ሳምንት ጨዋታ አርባምንጭ ከተማ ኢትዮጵያ ቡናን ድሬዳዋ ከተማ ደግሞ ባህርዳር ከተማን የሚገጥም ይሆናል ።